አዲሱ የካርታ ኅትመት በ15 ቀን ውስጥ ሥራ እንደሚጀምር ተገልጿል
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በመሬትና መሬት ነክ አገልግሎት ላይ ከጣለው ዕገዳ መካከል የጋራ መኖሪያ ንግድ ቤት ይዞታ ማረጋገጫ ካርታ ኅትመት፣ የዕግድና ዕገዳ መጣራት አገልግሎት ዕገዳ መነሳቱን አስታውቋል፡፡
የከተማ አስተዳደሩ ካቢኔ ከነሐሴ 7 ቀን 2013 ዓ.ም. ጀምሮ ለመሬት አስተዳደር ተቋማት፣ ለመሠረተ ልማት ቅንጅትና ግንባታ ፈቃድ ባለሥልጣን፣ እንዲሁም ለ11 ክፍለ ከተሞች አስተላልፎት በነበረው ድበዳቤ፣ የመሬትና መሬት ነክ አገልግሎቶች ላልተወሰነ ጊዜ ሙሉ በሙሉ እንዲቆሙ ውሳኔ አስተላልፎ እንደነበር ይታወሳል፡፡
የከተማ አስተዳደሩ ከተማ መሬት ልማትና አስተዳደር ቢሮ ጥር 2 ቀን 2014 ዓ.ም. ለ11ዱም ክፍለ ከተሞች በተጻፈ ደብዳቤ ዕገዳው መነሳቱን ሪፖርተር ያገኘው መረጃ ያመላክታል፡፡
በደብዳቤው መሠረት የጋራ መኖሪያና ንግድ ቤቶች የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ ኅትመትና የዕዳና ዕገዳ ማጠራት አገልግሎት መነሳቱን በመግለጽ ክፍለ ከተሞች አገልግሎት እንዲሰጡ ትዕዛዝ ተላልፏል፡፡
የቢሮው ኃላፊ አቶ ጀማል አልይ ከጥቂት ሳምንታት በፊት በሰጡት መግለጫ እንደተናገሩት፣ ከዚህ ቀደም የነበረው የይዞታ ካርታ ኅትመት የሚሠራው በማዕከል ቢሆንም፣ የመሬት ይዞታ የባለቤትነት ማረጋገጫ ሥርጭቱ የሚከናወነው በክፍላተ ከተሞች ነው፡፡
ኃላፊው ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ አዲሱ የካርታ ኅትመት ሙሉ በሙሉ በ15 ቀናት ውስጥ ሥራ ይጀምራል ብለዋል፡፡
በዚህም በክፍለ ከተሞቹ የሚሰራጩት ካርታዎች ለተለያዩ ሕገወጥ ድርጊቶች ተጋላጭ እንደነበሩ የገለጹ ሲሆን፣ በተጠቀሰው ወቅት ያላግባብ በየክፍለ ከተሞቹ ተሠራጭተው የሚገኙ ካርታዎች ለሕገወጥ ወረራ ተጋላጭ እንዳይሆኑ 472 ሺሕ ካርታዎች ተለይተው መሰብሰባቸውንና ካርታዎቹ በግለሰቦች እጅ ላይ የደረሱበት አጋጣሚ ይኖራል በሚል ጥርጣሬ ካርታዎቹ መምከናቸውን መናገራቸው ይታወሳል፡፡