የአዲስ አበባ ውኃና ፍሳሽ ባለሥልጣን፣ በበጀት ዓመቱ ስድስት ወራት ውስጥ 103.4 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ የጥራት ደረጃውን ያሟላ ውኃ አምርቶ ለማሠራጨት ካቀደው 88.8 በመቶ ማሳካቱን አስታወቀ፡፡ በእነዚሁ ወራትም 93.17 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ ውኃ አምርቶ ማሠራጨቱን አክሏል፡፡
የዘንድሮን የስድስት ወራት አፈጻጸምን የገመገመው ባለሥልጣኑ፣ በፍሳሽ ዘርፍም 19,490,567 ሜትር ኪዩብ በመስመር፣ 489,744 ሜትር ኪዩብ በግልና በተቋሙ ተሸከርካሪ በድምሩ ከ19.9 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ በላይ ፍሳሽ አሰባስቦ በማጣራት የዕቅዱን መቶ በመቶ ማከናወኑን ገልጿል፡፡
በገቢ አሰባሰብ በኩልም ባለፉት ስድስት ወራት 886 ሚሊዮን ብር ለመሰብሰብ አቅዶ ከ865 ሚሊዮን ብር በላይ ማለትም የዕቅዱን 98 በመቶ መሰብሰብ መቻሉን ተናግሯል፡፡
በከተማው የሥራ ዕድል ፈጠራ ቢሮ በየትምህርት ዘርፋቸው ተደራጅተው ለተላኩ ኢንተርፕራይዞችም የ67 ሚሊዮን ብር ፕሮጀክት ሥራ ትስስር መፍጠሩንም ባለሥልጣኑ አስታውቋል፡፡
የሥራ ዕድል ፈጠራና መረጃ ክፍል ኃላፊ አቶ ዋሲሁን ዘውዴ እንደገለጹት፣ ሥራ አጥ ወጣቶቹ ከተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች የተመረቁና በከተማው የሥራ ዕድል ፈጠራ ቢሮ ተደራጅተው የተላኩ ሲሆን፣ ወደ ሥራ ለማስገባት ቅድመ ዝግጅቱ በመጠናቀቅ ላይ ነው፡፡
ወጣቶቹ ስለሚሰማሩበት መስክ፣ ገለጻ፣ የተደረገላቸው ሲሆኑ የሚሠሩበትን ሳይት ምልከታ ላይ እንደሚገኙም አቶ ዋሲሁን አብራርተዋል፡፡
በባለሥልጣኑ የማኅበራዊ ትስስር ገጽ እንደተገለጸው፣ ኢንተርፕራይዞቹ ከሚሰማሩባቸው የሥራ መስኮች መካከል የውኃና ፍሳሽ መስመር ዝርጋታ፣ የአጥር፣ የመጸዳጃ ቤት፣ የማንሆል፣ የማማ፣ የጥበቃ ቤት ግንባታና የመሳሰሉት ፕሮጀክቶች ይገኙበታል፡፡