የወጣቶች ሥራ አጥነት መስፋፋት ሥነ ልቦናዊ ችግር ያመጣው መሆኑን፣ የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር በጥናት ማረጋገጡን አስታወቀ። በኢትዮጵያ በየዓመቱ ሁለት ሚሊዮን ዜጎች ሥራ ፈላጊ እንደሚሆኑ ያሳየው ጥናቱ፣ ይህም ወጣቶች ሥራ ለመፍጠር ያላቸው ሥነ ልቦናዊ ዝግጁነት የፈጠረው መሆኑን አመላክቷል።
የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ከዳቪድና ሊውስ ፓካርድ ፋውንዴሽን በተገኘ የገንዘብ ድጋፍ ከቢቢሲ ሚዲያ አክሽን ጋር በመተባበር፣ ከወጣቶች የሥራ ፈጠራ ሥነ ባህሪ ጋር በተገናኘ ያሉ ችግሮችን ለመለየት ያለመ ጥናት ማካሄዱን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታው አቶ ንጉሡ ጥላሁን ገልጸዋል።
በአምስት ክልሎች የተደረገው ጥናት ባለፉት አንድ ዓመት ተኩል መከናወኑንና ከ15 እስከ 29 የሆኑ ከሁለት ሺሕ በላይ ወጣቶችን ያካተተ መሆኑን፣ በተለይ ወጣቶች ሥራ መፍጠር እንዳይችሉ የሚያደርጋቸው ‹‹አልችልም›› ከሚል መነሻ መሆኑን በጥናቱ ማወቅ ተችሏል ብለዋል።
የአማራ፣ የኦሮሚያ፣ የሲዳማ፣ የደቡብና የሶማሌ ክልሎችን ያካተተው ጥናቱ፣ የገንዘብ አቅርቦት ከፍተኛ ችግር ቢሆንም፣ አስፈላጊው ገንዘብ ቀርቦ ሥልጠናና ክህሎት ሲዘጋጅም ወጣቶች በአብዛኛው ዝግጁ አለመሆናቸው ተመላክቷል።
በጥናቱ ከተካተቱት ከ2,000 በላይ ሰዎች ውስጥ የሥራ ተነሳሽነት የሌላቸው ከ80 በመቶ የሚበልጡ መሆናቸውን፣ ከዝግጁነት ባለፈ የአቅም ችግር እንዳለባቸው ለመለየት መቻሉ ተገልጿል።
የዳቪድና ሊውስ ፓካርድ የኢትዮጵያ የፕሮግራም ኃላፊ ወ/ሮ የምሥራች በላይነህ ለጥናቱ ከ200,000 ዶላር በላይ መውጣቱን ገልጸው፣ የጥናቱ ግኝት ለወጣቶች ራሱን የቻለ ስትራቴጂ መቀረፅ እንዳለበት ያመላከተ ነው ብለዋል።
በተጨማሪም የመንግሥት ተቋማትም ፖሊሲዎቻቸውንና የሥራ መሥፈርቶቻቸውን መፈተሽ፣ ወጣቶችን ማዕከል አድርገው መቅረፅ እንዳለባቸው ምክረ ሐሳብ ተቀምጧል ብለዋል።
የሥራ ፈጠራ ስትራቴጂው ለወጣቶች ተስማሚ አለመሆኑን የገለጹት አቶ ንጉሡ፣ በተለይ በመንግሥት ተቋማት አሠራርና ፖሊሲዎች ላይ ማሻሻያ ማድረግ አስፈላጊ መሆኑን አሳስበዋል።
ለዚህም ይረዳ ዘንድ ጥናቱን መነሻ በማድረግ የስትራቴጂ ዝግጅት መደረጉን ገልጸው፣ በዋነኝነት የወጣቶችን አቅም መገንባትና መረጃቸውን ማሳደግ ላይ ትኩረት አድርጎ ከሚዲያ አካላት ጋር ለመሥራት ያለመ ነው ብለዋል።
በተጨማሪም ለአዳዲስ ሥራ ፈጣሪዎች ፖሊሲ ቀረፃ፣ እንዲሁም ለአነስተኛና ለጥቃቅን ኢንተርፕራይዞች የፖሊሲ ማሻሻያዎች እንደሚደረጉ ጠቁመዋል።
ሚኒስቴሩ በ2013 በጀት ዓመት ከ3.4 ሚሊዮን በላይ ሰዎች የሥራ ዕድል መፍጠሩን፣ ከዚህም ውስጥ 66 በመቶ የሚሆነው ቋሚ የሥራ ዕድል መሆኑን ከሚኒስቴሩ የተገኘው መረጃ ያመለክታል። በ2014 ዓ.ም. ከ3.1 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑ ሰዎች የሥራ ዕድል ለመፍጠር የታቀደ ሲሆን፣ ከዚህም ውስጥ 80 በመቶ የሚሆነውን ቋሚ የሥራ ዕድል ለማድረግ ታስቧል።