መንግሥት የትምህርት ዘርፉን ለማሻሻል እንዲሁም በዘመናዊ ቴክኖሎጂ ለማገዝ እየሠራ ቢሆንም፣ ጥራቱን የጠበቀ የትምህርት አሰጣጥ ላይ ክፍተቶች እንዳሉ ከተለያዩ የዘርፉ ባለሙያዎች፣ ከምሁራንና ከትምህርት ሚኒስቴር በተደጋጋሚ ሲነገር ይሰማል፡፡ በተለይም በሥነ ምግባር የታነፁ ተማሪዎችን ለማፍራት የሚደረገው ጥረት ላይ ይህ ነው የሚባል ውጤት አለመታየቱ በተደጋጋሚ ተነግሯል፡፡
ከኩረጃ ጋር ያሉ ችግሮችን ለመቅረፍ የአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ አስተዳደር መምህራንና ተማሪዎች በተገኙበት ‹‹ኩረጃ ይብቃ›› (No More Cheating) በሚል መሪ ቃል ባለፍነው ሳምንት ውይይት አካሂዷል፡፡
የአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ትምህርት ጽሕፈት ቤት ዋና ሥራ አስፈጻሚ ወ/ሮ ሽታዬ መሐመድ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በክፍለ ከተማው ከ92 ሺሕ በላይ ተማሪዎች ይገኛሉ፡፡ እነዚህንም ተማሪዎች በሥነ ምግባር አንፆ በራሳቸው ቆመው እንዲሄዱ ለማስቻል ከታች መዋቅር ተዘርግቶ እየተሠራ ነው፡፡
በክፍለ ከተማው የሚገኙ ተማሪዎች ውጤታቸውን ለማሻሻልና ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ለማስቻል እየተሠራ መሆኑን የገለጹት ዋና ሥራ አስፈጻሚዋ፣ በተለይም በዘርፉ ላይ እንደ ማነቆ ሆኖ እየታየ ያለውን የእርስ በርስ ኩረጃ ለማስቀረት ከመምህራን ጋር እጅና ጓንት በመሆን እየተሠራ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡
ባለፉት ሦስት ዓመታትም የተማሪዎችን ውጤት ለማሻሻል የተለያዩ ሥራዎች መሠራታቸውን፣ የከተማ አስተዳደሩ ጉልህ ድርሻ መወጣቱን፣ ይህም በተማሪዎች ውጤት ላይ ሆነ በሥነ ምግባራቸው ላይ የተወሰነ ለውጥ እንዳመጣ ወ/ሮ ሽታዬ አክለው ገልጸዋል፡፡
የኩረጃን ችግር ለመቅረፍ ከርዕሰ መምህራንና ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት መደረጉን ያስታወሱት ወ/ሮ ሽታዬ፣ ተማሪዎች ትምህርታቸውን በአግባቡ በመከታተል እንዲሁም እርስ በርስ በመተጋገዝ የተጣለባቸውን ኃላፊነት መወጣት አለባቸው ብለዋል፡፡
በመንግሥት በኩል የሚሰጡ ማንኛውም ትምህርቶች ባክነው እንዳይቀሩ መዋቅር መዘርጋቱን፣ በተለይ ደግሞ በመምህራን ክፍተት ምክንያት የትምህርት ሥርዓቱ እንዳይበደል ለማድረግ ክፍለ ከተማው የራሱ አሠራር ዘርግቶ እየሠራ እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡
የተሠሩ ሥራዎችን አስመልክቶ ምን ዓይነት ውጤቶች ይኖሩታል፣ ምን ዓይነት ችግሮች ተቀርፈዋል፣ የሚለውን ለማወቅ ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት በየወሩ በመገናኘት ክትትል የሚደረግ መሆኑን አብራርተዋል፡፡
በተማሪዎች ላይ እየታየ ያለው ውጤት አነስተኛ መሆኑንና አብዛኛዎቹ ተማሪዎችም በራስ የመተማመን አቅማቸው ዝቅተኛ በመሆኑ ኩረጃን አማራጭ እንደሚያደርጉ፣ ይህንንም ለማወቅ ክፍለ ከተማው ጥናት ማካሄዱን የአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ትምህርት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ወ/ሮ ሳምራዊት ቅባቱ ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡
አብዛኛውን ተማሪዎች የክፍልም ሆነ አገር አቀፍ ፈተና በሚወስዱበት ጊዜ ኩረጃን ተማምነው እንደሚገቡ የገለጹት ኃላፊዋ፣ እነዚህንም ተማሪዎች ለመታደግና ያሉትን መሠረታዊ ችግሮች ለመፍታት ክፍለ ከተማው ከታች ጀምሮ እየሠራ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡
ሁለት ሺሕ የሚሆኑ መልካም ሥነ ምግባርና ውጤታማ የሆኑ እንዲሁም ኩረጃን ተማምነው የሚማሩ ተማሪዎች በውይይቱ ላይ መሳተፋቸውን፣ እነዚህም ተማሪዎች ኩረጃን ለማስቀረት በሚደረገው ትግል ላይ የበኩላቸውን ለመወጣት ቃል መግባታቸውን ወ/ሮ ሳምራዊት ገልጸዋል፡፡
እያንዳንዱ ተማሪ ምን ዓይነት ለውጥ አምጥቷል የሚለውን ለመፈተሽ ግልጽ የሆነ አሠራር መዘርጋቱን፣ በተለይም ውጤታቸው ጥሩ የሆኑ ተማሪዎች መልካም ሥነ ምግባር ካልተላበሱ ተማሪዎች ጋር በማገናኘት ሥነ ምግባር የማነፅ ሥራ እየተሠራ መሆኑን አክለዋል፡፡
ተማሪዎች በሥነ ምግባርም ሆነ በሌሎች ራሳቸውን ችለው እንዲቆሙ ከተደረገ በኋላ ፈተና እንዲፈተኑ የሚደረግ ሲሆን፣ በዚህም ምን ዓይነት ለውጦችን አምጥተዋል የሚለውን በቀላሉ ለማወቅ እንደሚያስችል ኃላፊዋ ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡
ከተማሪዎች ውጪም ብቃት ያላቸውን መምህራን ለማፍራት ክፍለ ከተማው ሥልጠናዎችን እየሰጠ እንደሚገኝ የሚናገሩት ኃላፊዋ፣ ይህም የነበረባቸውን የሙያ ክህሎት ከማሳደግ ባለፈ ውጤታማ ተማሪዎች ለማፍራት ይረዳቸዋል ብለዋል፡፡
ካደጉ አገሮች ተርታ ከሚመደቡ አገሮች ልምዶችን ወስደውና ዘመናዊ ቴክኖሎጂ ተጠቅመው ለተማሪዎቻቸው ልምዳቸውን እንዲያካፍሉ ለማድረግ እየተሠራ ነው፡፡
በውጤታቸው ዝቅተኛ የሆኑ ተማሪዎችን በመከታተል ውጤቱ የተበላሸው ከመምህሩ የትምህርት አሰጣጥ ችግር ነው? ወይስ ከተማሪው ንዝህላልነት? የሚለውን ለመለየት በተለያዩ ጊዜያት ግምገማ የሚካሄድ መሆኑን ወ/ሮ ሳምራዊት ተናግረዋል፡፡