Sunday, March 26, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ዝንቅሲኒማ በሐረርና ድሬዳዋ ከ70 ዓመት በፊት

ሲኒማ በሐረርና ድሬዳዋ ከ70 ዓመት በፊት

ቀን:

 በ1940ዎቹ በሐረርና በድሬዳዋ ከተሞች ፊልም ምሽት ላይ በአደባባይ፣  ማሳያው የቤት አውቶሞቢል ላይ ሆኖ ይታይ እንደነበር እነዚህ ፎቶዎች ምስክሮች ናቸው፡፡ ፎቶዎቹ አዲስ አበባ ከሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ ማህደሮች የተገኙ ናቸው፡፡

 

hjghj

  • ‹‹ታሪካዊት ኢትዮጵያ በካሜራ ሌንስ››

********

አዳምና ሔዋን

ቀዳማዊው ጽልመት ሲወርድ በዙሪያቸው

ቅጠሎች ደከሙ ሞገስ ሰልችቷቸው፤

በጠራው ፀጥታ ውበት አጋጥማቸው

ዘዴዎችዋን ሁሉ ገለጸላቸው፡፡

በጠራራው ፀሐይ መካነ ገነት

ፀሐይ ይሞቃሉ ወፍም መላእክት፤

አስተማረቻቸው ሰማያዊ ምክር

ከቃጠሎው ንዳድ ከሃሩር ሲሸሹ ከሞቃቱ አየር

ያዩት ነገር የለም ከህልም በስተቀር፡፡

እጆቻቸውንም ውበት ጠፋፈረች

እንዲበርድላቸው ምንጯ ውስጥ ነከረች

ቀኑም ዘመም ሲል ሲቃረብ ሌሊቱ፤

ወዲያው አንቀላፉ ቆነጃጅቶችም እንደሚተኙቱ፤

ከዚያም አረፍ ብላ ጥቂት እንደቆየች፤

ነቅታ ከአፈራቸው አይላ አበበች፡፡

  • ከማርጆሪ ፒክቶል (1883 እስከ 1922) ትርጉም በዳዊት ዘኪሮስ

***

‹‹ደባ ራሱን ስለት ድጉሱን››

ከጥንት ጀምሮ በቃል ሲነገር የሚኖረውን የአባቶቻችንን ተረት ብንመለከተው ብዙ የሚጠቅም ምክር እናገኝበታለን፡፡ በአርእስቱ እንደተነገረው ክፉ ሥራ መሥራት ጉዳቱ ለሠሪው ነው፡፡ ንብ ሌላውን አጠቃሁ ስትል በመርዟ ትነድፋለች፡፡ እሷም ይህን ክፋት ከሠራች በኋላ አንድ ደቂቃ ሳትቆይ ትሞታለች፡፡ የእሳት ራትም እንዲሁ መብራቱን ለማጥፋት ስትሞክር ተቃጥላ ራሷ ትጠፋለች፡፡ ትንኝ ሰው ዓይን ለማወክ ትገባና ሕይወቷን አጥታ ተጎትታ ትወጣለች፡፡ እንክርዳድን የዘራ እንክርዳድን ያመርታል ክፉ የሠራም ሰው በክፋቱ ይጠፋል፡፡ በሰው የሚድነው በምነቱና በቅንነቱ ብቻ ነው፡፡

  • አያሌው ተሰማ ዘብሔረ ጎጃም የካቲት 20 ቀን 1935 ዓ.ም.

*******

የሰው ነገርበችሎት ፊት

አንድ ሲራራ ነጋዴ መንገድ ሲሔድ ቆይቶ ቀን በምሳ ሰዓት ከአንድ ዛፍ ሥር አረፍ ብሎ ምሳውን ቆሎ ቆርጥሞና ውሃ ጠጥቶ ጉዞውን ሲቀጥል ሁለት መቶ ጠገራ ብር ረስቶ ሄደ። አንድ ገበሬ አግኝቶለት ያንን ገንዘብ ሊሰጠው ከኋላ እየሮጠ ተከተለውና ‹‹ሰውዬ ቆም ብህ ጠብቀኝ፤ ጥለኸው የሔድከው ገንዘብህን አግኝቼልሃለሁ፤›› አለው። ነጋዴውም ‹‹ያገኘኸው ገንዘብ ስንት ነው?›› ሲለው ‹‹ሁለት መቶ ብር›› አለው።

ነጋዴው ግን ‹‹እኔ የጠፋብኝ ገንዘብ ሦስት መቶ ብር ነው። አንዱን መቶ ብር የት ደብቀህ ነው ሁለት መቶ ብር የምትሰጠኝ። ሞልተህ ካላመጣህ አልቀበልህም እከስሃለሁ። እንዲህ በዋዛ አንላቀቅም›› አለው።

ገበሬውም ገንዘቡን እንደያዘ ወደ ኋላ ተመለሰ። ነጋዴው የመሠረተው የውሸት ክስ በይግባኝ ተይዞ ወደ አፄ ቴዎድሮስ ሲቀርብ የሁለቱን አባባል ካዳመጡ በኋላ ነጋዴውን ምን ያህል ገንዘብ ነው የጠፋህ? ሲሉት ‹‹ሦስት መቶ ጠገራ ብር ነው›› አላቸው።

ገበሬውንም ‹‹ምን ያህል ገንዘብ አገኘህ?›› ሲሉት ‹‹ሁለት መቶ ጠገራ ብር ብቻ ነው›› አለ። ከዚያ በኋላ ‹‹አንተ ነጋዴው ጠፋብኝ የምትለውን ሦስት መቶ ብር ከጣልህበት ቦታ ፈልገህ አግኝ። ሁለት መቶ ብር ያገኘኸው ገበሬ ደግሞ ሁለት መቶ ብር ጠፋኝ የሚል ሌላ ሰው እስከሚመጣ ድረስ ራስህ ልትጠቀምበት ትችላለህ›› ሲሉ ፈርደው ፋይሉ ተዘጋ።

  • መጋቤ አእላፍ መክብብ አጥናው ‹‹አምስተኛው ጉባኤየአባቶች ጨዋታ›› (2005 ዓ.ም.)

******

ዛራቱስትራና ባለፀጋዋ ኮከብ

‹‹ዛራቱስትራ የሠላሳ ዓመት ጐልማሳ በሆነ ጊዜ አገሩንና የአገሩንም ወንዞች ትቶ ወደ ተራራ ሄደ፡፡ በዚያም የገዛ ራሱን መንፈስና ብቸኝነቱን በመደሰት ምንም ስጋት ሳይሰማው አሥር ዓመት ኖረ፡፡ በመጨረሻ ልቡ ተመለሰ፡፡ አንድ ቀን ማለዳ ተነሣ፡፡ በፀሐይዋ ፊለፊት ቆሞ እንዲህ ሲል ተናገራት፡፡

ትልቅ ኮከብ ሆይ፤ ብርሃንሽን የምታድያቸው ባይኖሩሽ ኖሮ ደስታሽ ምን ይሆን ነበር፡፡ አሥር ዓመት ሙሉ በየዕለቱ እስከ ዋሻዬ ድረስ ትመጭ ነበር፡፡ እኔና አብረውኝ ያሉት ንስርና እባብ ባንኖር ኖሮ ስለ ብርሃንሽና ስለ ጉዞሽ ሐሳብ ይገባሽ ነበር፡፡ ግን እኛ በየጧቱ እንጠባበቅሽ ነበር፡፡ ተትረፍርፎ ካንቺ የሚፈሰውን ወሰድን፤ ስለሱም መረቅንሽ፡፡

እነሆ፣ ስለ ጥበቤ ሐሳብ ገባኝ፤ ብዙ ማር እንዳከማቸች ንብ ለመውሰድ የተዘረጉ እጆች አስፈለጉኝ፡፡ ወዲያ ለመስጠትና ለማደል እፈልጋለሁ፡፡ በሰዎች መካከል ያሉት ጠቢባን በሞኝነታቸው፤ ድሆችም በሀብታቸው እስኪደሰቱ ድረስ፡፡ በዚህ ዓላማ ምክንያት አሁን ቁልቁል መውረድ አለብኝ፡፡ ሁልጊዜ በየምሽቱ እንደምታደርጊው፣ በባሕሩ ማዶ አልፈሽ በታችኛው ዓለም ላሉት ብርሃን ለመስጠት እንደምትሄጅ፣ እጅግ ባለፀጋዋ ኮከብ ሆይ፡፡ እኔም እንዳንቺ ወደታች ‹‹መጥለቅ›› አለብኝ፤ የምወርድላቸው ሰዎች እንደሚሉት፡፡ ከመጠን በላይ የሆነውን ደስታ እንኳ ያለቅናት የምታይ፣ ሰላምን የተመላሽ ዓይን ሆይ፣ እንግዲህ መርቂኝ፡፡

ተርፎ ለመፍሰስ የሚፈልገውን ዋንጫ መርቂ፣ ውኃው ከሱ እንደ ወርቅ ይፈስ ዘንድ፤ የደስታሽንም ማንፀባረቅ (ሪፍሌክሽን) ወደ መላው ዓለም ይሸከምልሽ ዘንድ፡፡ እነሆ ይህ ዋንጫ እንደገና ባዶ ለመሆን ፈለገ፤ ዛራቱስትራም ዳግመኛ ሰው ለመሆን ተመኘ፡፡

  • እጓለ ገብረ ዮሐንስ ‹‹የከፍተኛ ትምህርት ዘይቤ›› (1956)

**********

‹‹ተሜ ተቀምጬ ልስጥህ?››

አንድ የቅኔ ተማሪ ለእራት የሚሆነውን ቁራሽ ለመለመን ወደ ገጠር ነዋሪዎች /ወደ መንደር/ ብቅ ይልና ‹‹በእንተስማ ለማርያም ስለ ቸሩ እግዚአብሔር ብለው›› ይልና ይለምናል፡፡ ቁራሽ በሚለምንበት መንደር ‹‹ተቀምጬ›› የሚባል የምግብ ዓይነት ነበርና አንዲት ሴት ወይዘሮ እንጀራ አልጋገረች ኖሮ ‹‹ተማሪ እንጀራ አልጋገርኩምና ተቀምጬ ልስጥህ?›› ትለዋለች፡፡ ተማሪውም መልሶ ‹‹ኧረ እመይቴ የሚዘክሩኝስ ከሆነ ተኝተውም ቢሆን ቢሰጡኝ አልጠላም፤›› አላቸው ይባላል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

ለፋይናንስ ዘርፉ ብቃት ያለው የሰው ኃይል የማፍራት የቤት ሥራን የማቃለል ጅማሮ

የአገሪቱ የፋይናንስ ዘርፍ እያደገ ለመሆኑ ከሚቀርቡ ማስረጃዎች ውስጥ  የግል...

የምድር ባቡርን የሚያነቃቃው የመንግሥት ውሳኔ

በኢትዮጵያ ወደብ አልባነት ላይ የተደመረውን የሎጀስቲክስ ችግር ለመፍታት ግዙፍ...

የፓርላማ አባላት ስለሰላም ስምምነቱ አፈጻጸም ግልጽ መረጃ የለንም አሉ

‹‹ሕወሓትን ለፍረጃ አብቅተውት የነበሩ ጉዳዮች በአብዛኛው መልክ ይዘዋል›› ሬድዋን...