የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን የቅዱስ ሲኖዶስ አባላትና የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ፣ በቅዱስ ሲኖዶስ አዳራሽ ውይይት ካደረጉ በኋላ ስምምነት በተደረሰባቸው ጉዳዮች ላይ የጋራ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡
ማክሰኞ የካቲት 8 ቀን 2014 ዓ.ም. በተሰጠ የጋራ መግለጫ የመስቀል አደባባይና የጃንሜዳ ጥምቀተ ባህር ጥያቄዎችን የሚመልስ የጋራ ኮሚቴ ለማቋቋም፣ ከስምምነት መደረሱ ይፋ ተደርጓል፡፡
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስና የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ባደረጉት የጋራ ውይይት፣ የመስቀል አደባባይና የጃንሜዳ ጥምቀተ ባህር ጥያቄዎችን ለመፍታት መግባባት ላይ መድረሳቸውን አስታውቀዋል፡፡
የጋራ መግለጫውን በንባብ ያሰሙት የሲዳማ፣ የጌዴኦ፣ የአማሮና የቡርጂ ዞኖች አኅጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊው ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ ሲሆኑ፣ መግለጫው የተመጠነና ሁለቱ ወገኖች ያደረጉት መግባባት ላይ ያተኮረ ነበር፡፡
በዚሁ መግለጫ እንደተመለከተው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ያነሳቻቸውን የመስቀል አደባባይና የጃንሜዳ ጥምቀተ ባህርን የተመለከቱ ጥያቄዎች፣ በጋራ ኮሚቴ በውይይት ለመፍታት፣ ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጋር ስምምነት ላይ ደርሳለች፡፡
ሁለቱ ወገኖች ቀጣይ ውይይቶቻቸውን መሠረት በማድረግ፣ በአጭር ጊዜና በማያዳግም ሁኔታ፣ የመስቀል አደባባይና የጃንሜዳ ጥምቀተ ባህር ጥያቄዎች ላይ ዕልባት እንደሚሰጡ በጋራ በሰጡት መግለጫቸው አስታውቀዋል፡