በቅርቡ በአዲስ አበባ ከተማ በተካሄደው 35ኛው የአፍሪካ ኅብረት የመሪዎች ጉባዔ የኅብረቱ የሥራ ቋንቋ እንዲሆን በተደረገው ስዋሂሊ ቋንቋ፣ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ለማስተማር እንዲችል ከዳሬሰላም ዩኒቨርሲቲ ጋር ተስማምቷል፡፡
የሁለቱ ዩኒቨርሲቲዎች ስምምነት በዋናነት የሚያተኩረው የስዋሂሊን ቋንቋ በምሥራቅ አፍሪካ ከሚነገሩት ቋንቋዎች ውስጥ መሪ የመግባቢያ ቋንቋ ለማድረግ ሲሆን፣ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲም ቋንቋውን በመጀመሪያ ዲግሪና በሁለተኛ ዲግሪ መርሐ ግብሮች ለማስጀመር ስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡
አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በትስስር ገጹ እንዳስታወቀው፣ ስምምነቱ በተጨማሪም የአካዴሚክና የምርምር መርሐ ግብሮችን በማሳደግና በመተግበር ኢኮኖሚያዊና ባህላዊ ዕድገትን በሁለቱ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት መካከል ለማነቃቃት ነው፡፡
የስዋሂሊኛ ቋንቋን ከማስፋፋት ባለፈም በሁለቱ ዩኒቨርሲቲዎች መካከል የሁለትዮሽ የአካዴሚክ መርሐ ግብሮችን ማስፋፋት፣ የሥልጠናና የስታፍ ልምድ ልውውጥ ማድረግ፣ የምርምር ትብብርና የተማሪዎች ክትትልን ማጠናከር፣ እንዲሁም የፒኤችዲ ዲዘርቴሽን የምርምር ተግባር ትብብርን እንደሚያጠቃልል ተገልጿል፡፡
ስምምነቱም ለአምስት ዓመታት የሚቆይ ሲሆን፣ እንደአስፈላጊነቱም በሁለቱ ዩኒቨርሲቲዎች መልካም ፈቃደኝነት መሠረት የሚታደስ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡
የስዋሂሊ ቋንቋን ትምህርት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ለማስጀመር የመግባቢያ ሰነዱን የተፈራረሙት የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ጣሰው ወልደሃና (ፕሮፌሰር) እና የዳሬሰላም ዩኒቨርሲቲ ምክትል ቻንስለር ዊሊያም አናንጊሴ (ፕሮፌሰር) ናቸው፡፡
በአፍሪካ ከ100 ሚሊዮን በላይ ተናጋሪዎች ያሉት ስዋሂሊ፣ የአፍሪካ ኅብረት የሥራ ቋንቋው እንዲሆን የቀረበለትን የውሳኔ ሐሳብ ያፀደቀው የታንዛኒያ ምክትል ፕሬዚዳንት ፊሊፕ ምፓንጎ ለኅብረቱ ያቀረቡትን ጥያቄ ተከትሎ ነው።
በተለያዩ ማኅበረሰቦች የምሥራቅ አፍሪካ ማኅበረሰብና ደቡባዊ አፍሪካ የልማት ማኅበረሰብን ጨምሮ ባገልግሎት ላይ ያለው ኪስዋሂሊ (የስዋሂሊ ሌላኛው መጠርያ)፣ ቀደም ባሉት ዘመናት የተለያዩ የአፍሪካ መሪዎች የመላው አፍሪካ ቋንቋ እንዲሆን ግፊት ሲያደርጉ መቆየታቸው ይታወቃል።
በሥነ ልሳን ምሁራን ጥናት መሠረት መነሻው ምሥራቅ አፍሪካ የሆነው የኪስዋሂሊ ቋንቋ በ14 አገሮች ማለትም በኬንያ፣ ሶማሊያ፣ ደቡብ ሱዳን፣ ታንዛኒያ፣ ዑጋንዳ፣ ሩዋንዳ፣ ቡሩንዲ፣ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ፣ ሞዛምቢክ፣ ማላዊ፣ ዛምቢያ፣ ኮሞሮስ እና በመካከለኛው ምሥራቅ እስከ ኦማን እና የመን ድረስ ይነገራል፡፡
የደቡባዊ አፍሪካ አገሮች ደቡብ አፍሪካና ቦትስዋና በትምህርት ቤቶች እያስተማሩበት መሆኑን ናሚቢያና ሌሎችም እያሰቡበት መሆኑን ተገልጿል፡፡
በኢትዮጵያ በ1950ዎቹ መገባደጃ ብሔራዊው የሬዲዮ ጣቢያ በስዋሂሊ ቋንቋ ሥርጭት እንደነበረው በወቅቱ የወጣ የሬዲዮና ቴሌቪዥን መርሐ ግብር ያሳያል፡፡
በምሕፃሩ ዩኔስኮ የሚባለው የተባበሩት መንግሥታት የትምህርት የሳይንስና የባህል ድርጅት፣ ሰኔ 30 ቀን (ጁላይ 7) የዓለም ኪስዋሂሊ ቋንቋ ቀን ብሎ መሰየሙና እየተከበረ መሆኑ ይታወቃል