– የኢትዮጵያ ፐልፕና ወረቀት አክሲዮን ማኅበር ኪሳራ ደርሶበታል
በማኑፋክቸሪንግ፣ እንዲሁም በንግድና አገልግሎት ዘርፍ የተሰማሩ አሥር የመንግሥት የልማት ድርጅቶች በስድስት ወራት ውስጥ 7.1 ቢሊዮን ብር ገቢ ማግኘታቸውን፣ የመንግሥት የልማት ድርጅቶች አስተዳደር ኤጀንሲ አስታወቀ፡፡
በማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ የተሰማሩት ድርጅቶች ማለትም የትምህርት መሣሪያዎች ማምረቻና ማከፋፈያ ድርጅት፣ ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ድርጅት፣ ብሔራዊ አልኮልና አረቄ ፋብሪካ፣ ብሔራዊ የእንስሳት ጤና ጥበቃ ኢንስቲትዩት በአጠቃላይ 1.2 ቢሊዮን ብር ገቢ ማግኘታቸው ታውቋል፡፡
በ2014 በጀት ዓመት የመጀመሪያ ስድስት ወራት ውስጥ በማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ የተሰማሩት አራቱ የልማት ድርጅቶች፣ 1.5 ቢሊዮን ብር ጠቅላላ ገቢ ለማግኘት አቅደው 1.2 ቢሊዮን ብር ገቢ ማስመዝገባቸው ታውቋል፡፡
በስድስት ወራት ውስጥ ከታክስ በፊት ለማግኘት ያቀዱት ትርፍ 388 ሚሊዮን ሲሆን፣ ከ400 ሚሊዮን ብር በላይ ማግኘት መቻላቸው ተገልጿል፡፡ በአጠቃላይ ከተገኘው የ403.8 ሚሊዮን ብር ትርፍ ውስጥ ብሔራዊ አልኮልና አረቄ ፋብሪካ 138.8 ሚሊዮን ብር በማትረፍ 34.5 በመቶ ድርሻ ይዟል ተብሏል፡፡
ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ድርጅት 107 ሚሊዮን ብር ያተረፈ መሆኑ፣ የትምህርት መሣሪያዎች ማምረቻና ማከፋፈያ ድርጅት 83 ሚሊዮን ብር ትርፍ ማግኘቱ፣ በአንፃሩ የኢትዮጵያ ፐልፕና ወረቀት አክሲዮን ማኅበር የ394 ሺሕ ብር ኪሳራ እንደደረሰበት ተጠቁሟል፡፡
በበጀት ዓመቱ አጋማሽ በንግድ፣ የሆቴልና ቱሪዝም አገልግሎት በመስጠት በመንግሥት የልማት ድርጅቶች ይዞታ አስተዳደር ሥር የሚገኙ በንግድና አገልግሎት ዘርፍ የተሰማሩ ስድስት የልማት ድርጅቶች ደግሞ፣ በድምሩ 9.2 ቢሊዮን ብር ገቢ ለማግኘት አቅደው 5.9 ቢሊዮን ብር ማግኘታቸውን አስተዳደሩ አስታውቋል፡፡
በንግድና አገልግሎት ዘርፍ የተሰማሩት የልማት ድርጅቶች የኢትዮጵያ ንግድ ሥራዎች ኮርፖሬሽን፣ የኢትዮጵያ ቱሪስት ንግድ ሥራ ድርጅት፣ የፍልውኃ አገልግሎት ድርጅት፣ ግዮን ሆቴል ድርጅት፣ ገነት ሆቴልና የኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ግብዓቶች ልማት ድርጅት ሲሆኑ በስድስት ወራት ውስጥ ያገኙት ትርፍም 611 ሚሊዮን ብር ነው ተብሏል፡፡
የኢትዮጵ ንግድ ሥራዎች ኮርፖሬሽን 3.1 ቢሊዮን ብር ገቢ በማግኘትና 350 ሚሊዮን ብር በማትረፍ ከፍተኛውን ድርሻ ሲይዝ፣ የኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ግብዓቶች ልማት ድርጅት ብር 2.2 ቢሊዮን ገቢ በማግኘት 176 ሚሊዮን ብር ትርፍ ማግኘቱ ተወስቷል፡፡
በአጠቃላይ አሥራ አንዱ ድርጅቶች ካገኙት ገቢ ውስጥ 7.7 ሚሊዮን ዶላር የሚሆነው የብሔራዊ አልኮልና አረቄ ፋብሪካ፣ ብሔራዊ የእንስሳት ጤና ጥበቃ ኢንስቲትዩት፣ የኢትዮጵያ ቱሪስት ንግድ ሥራ ድርጅትና የኢትዮጵያ ንግድ ሥራዎች ኮርፖሬሽን ወደ ውጭ ከላኳቸው ምርትና አገልግሎቶች የተገኘ መሆኑ ተገልጿል፡፡
በማኑፋክቸሪንግና በንግድና ኢንቨስትመንት የተሰማሩት ድርጅቶች ያገኙት የውጭ ምንዛሪ ገቢ በ2013 በጀት ዓመት የመጀመሪያ ስድስት ወራት ውስጥ፣ በንግድና አገልግሎት ዘርፍ ብቻ የተሰማሩ አራት ድርጅቶች ካገኙት የ9.09 ሚሊዮን ዶላር አንፃር ወደ ሁለት ሚሊዮን ዶላር የሚጠጋ ቅናሽ እንደታየበት ተመልክቷል።