ጅማሮውን በሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም አድርጎ ከዘጠኝ ሳምንታት በኋላ ወደ ድሬዳዋ አምርቶ ውድድሩን እያከናወነ የሚገኘው ቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ፣ ቀጣዩ የጨዋታ መርሐ ግብር በአዳማ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም እንደሚሆን ታውቋል፡፡
አወዳዳሪው አካል አዳማ ከተማ የፕሪሚየር ሊጉን ጨዋታ እንዲያስተናግዱ ከተመረጡ ከተሞች አንዷ እንደነበረች፣ ይሁንና ከስፖርት መሠረተ ልማት አለመሟላት ጋር ተያይዞ የአስተናጋጅነቱን ዕድል ፈቃደኛ ለሆኑ ሌሎች ከተሞች ለመስጠት ወስኖ የነበረ መሆኑ አይዘነጋም፡፡
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አክሲዮን ማኅበር የካቲት 11 ቀን 2014 ዓ.ም. ባካሄደው ስብሰባ፣ የአዳማ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም 16ኛውን ሳምንት ጨምሮ ቀጣይ ውድድሮችን እንዲያስተናግድ ወስኗል፡፡ ማኅበሩ ይሁንታ የሰጠው ዩኒቨርሲቲው ሜዳውን በሚመለከት ቀደም ሲል እንደ ክፍተት የቀረበለትን ቅድመ ሁኔታ እንደሚያሟላ በመስማማቱ እንደሆነ በማኅበራዊ ትስስር ገጹ ይፋ አድርጓል፡፡
በሌላ በኩል ማንነታቸው እንዲገለጽ ያልፈለጉ የሪፖርተር ምንጮች፣ አክሲዮን ማኅበሩ በተለይም ከጨዋታ ሜዳ ጥራት ጋር በተያያዘ ዩኒቨርሲቲዎች ባስገነቧቸው ስታዲየሞች ውድድሩን ማስቀጠል፣ አሊያም ውድድሩን ማቋረጥ ካልሆነ ሌላ አማራጭ እንደሌለው ነው የሚናገሩት፡፡
አክሲዮን ማኅበሩ በዚህ ዓመት የሚደረገውን የፕሪሚየር ሊግ ውድድር እንዲያስተናግዱ ቀደም ሲል የመረጣቸው ከተሞች ሐዋሳ፣ አዳማ፣ ድሬዳዋ፣ ጅማ፣ ባህር ዳርና አዲስ አበባ እንደነበሩ መግለጹ አይነጋም፡፡ ይሁንና ውድድሩ በሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ለዘጠኝ ሳምንት ያህል ከተካሄደ በኋላ፣ ቀጣዮቹ ውድድሮች በአዳማ መካሄድ ሲገባቸው ወደ ድሬዳዋ እንዲያመራ የተደረገውም የአዳማ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ውድድሩን ማስተናገድ የሚያስችል መሠረተ ልማት ማሟላት ባለመቻሉ እንደሆነ ጭምር የሪፖርተር ምንጮች ይገልጻሉ፡፡
የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) ነባሩን የአዲስ አበባ ስታዲየምን ጨምሮ፣ ከፍተኛ ወጪ ወጥቶባቸው የተገነቡ ስታዲየሞች በሙሉ የዓለም አቀፉን ዝቅተኛ መሥፈርት የሚያሟሉ ባለመሆናቸው፣ አኅጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ውድድሮችን ማስተናገድ እንደማይችሉ ክልከላ የተደረገባቸው ናቸው፡፡
በሌላ በኩል ከውድድር ሜዳዎች ጥራት ጋር በተያያዘ ችግር የገጠመው የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ፣ ከጥቂት ክለቦች በስተቀር በአሁኑ ወቅት ብዙዎቹ ክለቦች የተጫዋቾችን ወርኃዊ ክፍያ መክፈል እየቻሉ አለመሆኑ መዘገባችን ይታወቃል፡፡