Friday, March 24, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ዜናመንግሥት የቀይ ባህር ትብብር መድረክ አግላይነትን እንደሚቃወም አስታወቀ

መንግሥት የቀይ ባህር ትብብር መድረክ አግላይነትን እንደሚቃወም አስታወቀ

ቀን:

የቀይ ባህር ፎረም በሚል ስያሜ ለመጀመርያ ጊዜ በግብፅና በሳዑዲ ዓረቢያ አነሳሽነት እ.ኤ.አ. በ2019 እንደተመሠረተ የሚነገርለት የቀይ ባህር ትብብር መድረክ፣ ኢትዮጵያን ያገለለ በመሆኑ እንደሚቃወመው መንግሥት አስታወቀ፡፡

ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን በቅርቡ በጀርመን ሙኒክ በተካሄደው 58ኛው የፀጥታ ጉባዔ ላይ፣ የአፍሪካ ቀንድና የቀይ ባህር ቀጣና ካላቸው መልከዓ ምድራዊ አቀማመጥ ባለፈ የጋራ የሆኑ ችግሮች የሚስተዋሉባቸው በመሆናቸው፣ ሁሉን አቀፍ ትብብር እንደሚያስልጋቸው ማብራሪያ መስጠታቸውን፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ዲና ሙፍቲ (አምባሳደር) በሳምንታዊ ጋዜጣዊ መግለጫቸው አስረድተዋል፡፡

በቀጣናው በዋነኝነት ዓለም አቀፍ ትብብር የሚስፈልጋቸው የሽብርተኝነት፣ የሕገወጥ የሰዎችና የመሣሪያ ዝውውር፣ እንዲሁም ቀጣናዊ የኢኮኖሚ ትብብር ኢትዮጵያን የሚመለከቱና የሚነካኩ በመሆናቸው፣ በችግር አፈታት ረገድ የኢትዮጵያ ሚና ከባድ እንደሆነና አግላይነቱ አግባብ አለመሆኑን ቃል አቀባዩ አስረድተዋል፡፡

በፀጥታና በሰላም ጉዳይ ላይ እንደሚያተኩር ታስቦ በግብፅናሳዑዲ ዓረቢያ ዋና አነሳሽነት እንደተመሠረተ የሚነገርለት የቀይ ባህር ፎረም፣ በሌላ ዓላማው ኢትዮጵያን ከቀይ በህር ጂኦፖለቲካ የማራቅናከበባ ውስጥ የማስገባት ፍላጎት እንዳለው የጂኦፖለቲካ ተንታኞች  ይናገራሉ፡፡

ትብብሩ በአውሮፓ ኅብረት ጭምር የቀጣናውን ችግር ይፈታል በሚል ተስፋ የተጣለበት ቢሆንም፣ በርካቶች የቀይ ባህር ትብብር ፎረም ሳዑዲ ዓረቢያና ግብፅ በቀጣናው ትልቅ ሚና ያላቸውን ኢትዮጵያ፣ ሶማሌላንድ፣ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስና ቱርክን የመሳሰሉ አገሮች ሳያካትት መዋቀሩ በቀጣናው ሌላ የሥጋት ምንጭ ሊሆን  እንደሚችልም ያስረዳሉ፡፡

የትብብር ፎረሙ ግብፅ፣ ሳዑዲ ዓረቢያ፣ ዮርዳኖስ፣ የመን፣ ሱዳን፣ ጂቡቲና ሶማሊያን ያካተተ ቢሆንም፣ ‹‹ኢትዮጵያን ገሸሽ አድርገው ከመሠረቱ አገሮች ጋር በቀጣናው እኩል ጉዳይ አለን፤›› ሲሉ ቃል አቀባዩ ተናግረዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ባለፈው ሳምንት መጀመርያ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ባደረጉት ማብራሪያ፣ ቶፊቅ አብዱላሂ (ዶ/ር) የተባሉ የምክር ቤት አባል የቀይ ባህር ትብብር መድረክ በቀጣናው ከፍኛ የሆነ የንግድ ዝውውር በሚደረግበት ከባቢ ላይ የተመሠረተ ከመሆኑም በላይ፣ ኢትዮጵያን የማግለልና የማዳካም ተልዕኮ እንዳለው በመጠቆም፣ መንግሥት ምን ዓይነት እንቅስቃሴ እያደረገ ነው ሲሉ ጠይቀዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሰጡት ምላሽ፣ ‹‹ወፏ የተሰበረ ቅርንጫፍ ላይ የምታርፈው ዛፉን ተማምና አይደለም፣ የምትበርበትን ክንፍ ተማምና ነው፤›› ብለው፣ ‹‹ኢትዮጵያ ዛሬ ቀይ ባህር ትላለች፣ ነገር ግን አትጠራጠሩ ከ10 እና 15 ዓመታት በኋላ በሌሎች ራቅ ባሉ አገሮች ጉዳዮችም ጥቅም አለኝ ብላ ትነሳለች፤›› ሲሉ አስረድተዋል፡፡  በመሆኑም አሁን ኢትዮጵያን የያዛት የደኅንነትና የሰላም ችግር ሲስተካከል ዕይታው በዚያው ልክ ይስተካከላል ብለዋል፡፡

ቀይ ባህርን በሚመለከት የተመሠረተው ፎረም ሰላም ለማምጣት ከሆነ ኢትዮጵያ የሌለችበትን ሰላም ማረጋገጥ ከባድ እንደሆነ በመጥቀስ፣ ‹‹ከ110 ሚሊዮን ሕዝብ ውስጥ አሥር ሚሊዮን የሚሆነው እንኳ ከፈሰሰ መከራ ያመጣል፡፡ ስለዚህ ሰላም የሚፈልግ ኃይል በሰላም መሥራት ይኖርበታል፣ ይጠቅመዋል ብለን እናምናለን፣ ነገር ግን ጊዜው እያየ ይፈታዋል፤›› ሲሉ ተናግረዋል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

[ክቡር ሚኒስትሩ ከሚያከብሯቸው አንድ የቀድሞ ጉምቱ ፖለቲከኛ ስልክ ተደውሎላቸው እያወሩ ነው]

አንዳንድ ነገሮች ቢያሳስቡኝ ነው ቀጠሮ ሳልይዝ ላወራህ የፈለኩት ክቡር...

የትግራይ ክልል የሽግግር አስተዳደር ምሥረታና የሰላም ስምምነቱ ሒደት

በትግራይ ክልል ጊዜያዊ የሽግግር መንግሥት ለመመሥረት ደፋ ቀና እየተባለ...

ጥራዝ ነጠቅነት!

ከሜክሲኮ ወደ ጀሞ እየሄድን ነው፡፡ የተሳፈርንበት አሮጌ ሚኒባስ ታክሲ...