Friday, June 2, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ተሟገትዓድዋዊ መንፈስ ዕውን ዘልቆናል?

ዓድዋዊ መንፈስ ዕውን ዘልቆናል?

ቀን:

በበቀለ ሹሜ

ሀ) በዘንድሮው የዓድዋ አካባበር የተፈጠረው ጫጫታ ሲመዘን

አገራዊ ምክክር ለማድረግ የምንሰናዳው እንደ አንድ አገር ለመንቀሳቀስ አስፈላጊ በሆኑ መሠረታዊ ጉዳዮችና አቋሞች ላይ በአግባቡ ለመግባባት እንድንችል እንጂ፣ የአስተሳሰብንና የአመለካከት ብዝኃነትን አጥፍተን በአንድ ቦይ እንድንፈስ አይደለም፡፡ ያንን ብንፈልገውም ማድረግ አንችልም፡፡ የዚያ ዓይነት ጥረትም አይጠቅመንም፡፡ የዓድዋ ተጋድሎን ለዛሬ አገራዊ ተልዕኳችን ትልቅ መማሪያ ለመሆን ያበቃው በምኒልክ መመራቱ ወይም በታሪከኛ ድል መደምደሙ አይደለም፡፡ ታሪከኛው ድል የተገኘው የውስጥ ቅራኔ፣ ቁርሾና ቅሬታ የነበራቸው ወገኖች ከውስጥ ጣጣቸው አገርን አስበልጠው በአንድ ላይና በቁርጠኝነት ጠላታቸውን በመዋጋታቸው ነው፡፡ የዓድዋ ‹‹ተጋድሎ›› እና ‹‹ድል›› ዋና አስተማሪነት ያለው እዚህ ላይ ነው (የጫጫታ ስሜቶች ከበረዱ በኋላ ይህንን ጉዳይ ማንሳቴ ሆን ብዬ ነው፡፡ አዕምሮ ሚዛናዊ ነጥቦችን ለመቆንጠጥ እንዳይችል የስሜት ፍላት ማወኩን ከልምዴ ስለማውቅ)፡፡

የውስጥ አለመግባባቶችን ትተን በአገራዊ ህልውና ላይ መረባረብን የጠየቀ ተግባር በ1888 ዓ.ም. እንደነበረብን ሁሉ፣ ዛሬም ለአገራዊ ህልውናችን ግድ የሆኑ ዘርፈ ብዙ የርብርብ ተግባሮች አሉብን፡፡ ትናንትና የዓድዋው ፀረ ወረራ ተልዕኮ ከምኒልክ ጋር ቁርሾና አለመግባባት የነበራቸውን ሁሉ እንደፈለገና እንዳንቀሳቀሰ ሁሉ፣ የዛሬውም አገራዊ ተልዕኮ ከዓብይና ከብልፅግና ፓርቲ ጋር የማይጣጣሙ ኢትዮጵያውያንን ሁሉ ሽቷል፡፡ የዓድዋ መንፈስ ከገባንና በዚያ መንፈስ ውስጥ ለኢትዮጵያችን ህልውናና ግስጋሴ የሚካሄደውን ተጋድሎ የማጠናከር ሥራ እየሠራን ከሆነ፣ ለኢትዮጵያ መቆምንና መዋደቅን ዋና መሥፈርት አድርገን በፖለቲካ አስተሳሰብ የተለያዩ ኢትዮጵያዊ ቡድኖችን ሁሉ ለማስተባበር እየሠራን ነው ማለት ነው፡፡ ይህም ብቻ አይደለም፣ ከተባበሩት የርብርብ ኃይሎች ውስጥ እየተሸረፉ ወደ ፅንፍ አፈንጋጭነትና አኩራፊነት እንዳይሄዱ መንከባከብ ልባችንና ተግባራችን ውስጥ አለ ማለት ነው፡፡ በአፈንጋጭነት፣ በአኩራፊነትና በአፍራሽነት ውስጥ ከተሰማሩትም ውስጥ እንዲሁ በብልኃት እየሳብን የአገራዊ ግንባታውን ሠፈር የማደርጀት አድማስ ያለው ሥራ እንሠራለን ማለታችንም ነው፡፡ ይህ ተግባር አገር ወዳድ ነን የምንል ፖለቲከኞችና የሚዲያ ሰዎች ሁሉ ኃላፊነት ነው፡፡ የተግባሩ አንገብጋቢነትና ትልቅነት በዚች ታህል ቋንቋ መገለጽ የሚበቃውም አይደለም፡፡ ያለንበት የሽግግር ወቅት እንደመሆኑ፣ ውስጣዊ ወረራ ሰበብ ሆኖት የተንተረከከውን አገራዊ ኅብረት ለመሰነጣጠቅ/ለማኮማተር ፅንፈኞች ሌት ተቀን እንደ መልፋታቸው፣ ለኢትዮጵያ በማሰብ ከእኛ በላይ ለአሳር ያሉ ቦጭራቆችም በፉለላቸው በአገር ወዳዶች ሠፈር ውስጥ ገፍታሪ ጫጫታ እየፈጠሩ ፅንፈኞችን እየጠቀሙ እንደ መሆናቸው፣ አገር ወዳዶች ያለባቸው ኃላፊነት፣ ለአፍታም በዕይታ መቦዝ የማይገባው ድርብርብ ኃላፊነት ነው፡፡

በዓድዋዊ ዓውደ ሰፊነት ብሂል የምናካሂደው አገራዊ ርብርብን የማበራከት እንቅስቃሴ ገጾች በጣም ብዙ ናቸው፡፡ ታሪክን እንውሰድ፣ በኢትዮጵያ ታሪክ ላይ ስለመግባባት ስናወራ እንደ አገረ ኢትዮጵያ ያቆመንንና ያፀናንን የጋራ የታሪክ ፈትል ለይቶ ስለመጨበጥ ማውራታችን እንጂ፣ በታሪክ ሐተታዎች ሁሉ እንስማማለን ማለት አይደለም፡፡ በዋና የታሪክ ፈትላችን ላይ እንኳ በአሁኑ ደረጃ ላይ ‹‹ይሁን እስኪ›› የሚሉና ቃር የሚሰማቸው መኖራቸው አይቀርም (ቃሩ በአፄዎች ውዳሴ ውስጥ የኖሩትንም በአፄዎች ጠል ትርክት ውስጥ የኖሩትንም ይመለከታል፡፡) መግባባታችን እየዳበረ የጋራ የታሪክ ገመዳችንም እየወፈረ የሚሄደው በጊዜ ሒደት ውስጥ ነው፡፡ የአገር ግንባታችን ብሶትንና መርምኮምን እያመናመነ (በአገር መኩራትንና በኑሮ መሻሻልን እያፋፋ) ሲሄድ ነው፡፡

ከታሪክ ውስጥ አንድ ነገር መዘን እንይ፣ የዓድዋና የምኒልክን ግንኙነት፡፡ የዓድዋ ዘመቻ ግዙፍ ሠራዊት የከተተው በምኒልክ ንጉሠ ነገሥታዊ ጥሪና መሪነት አማካይነት መሆኑን፣ ማናችንም እንዳልነበር ልናደርገው አንችልም፡፡ የጦርነቱ ፈጣን ድልም የዕልፍ አዕላፋ ቆራጥ ጀግንነትና የብልህ ታክቲክ ቅንብር ውጤት ነው፡፡ በብልህ የጦር አመራር ውስጥ የድርሻ ማበላለጥ እናደርግ እንደሆን እንጂ፣ ምኒልክንና ጣይቱን አግንነን የጦር አበጋዞችን ሚና እንዳልነበር ልናደርግ እንደማንችል ሁሉ፣ የጦር አበጋዞቹን ሚና አግዝፈንም የምኒልክንና የጣይቱን ሚና ልናኮስስ አንችልም፡፡ የምኒልክ ነገር ከዚህም አልፎ ሄዷል፡፡ በዓድዋ ድል የታየው የነጭ ቅኝ ግዛታዊ ወረራ በጥቁር መሸነፍ በዓለም ላይ ከአፅናፍ አፅናፍ ሲናኝ፣ ለኢትዮጵያ/ለዓድዋ ድል የምኒልክ ስም ምትክ ወይም ተለዋጭ መግለጫ ሆኖ አገልግሏል፡፡ ‹‹አስገራሚው የምኒልክ ድል!›› እየተባለ ሲወሳና ሲጻፍ ስለኢትዮጵያውያን ድል መወሳቱ ነው፡፡ ይህ ምኒልክን የኢትዮጵያ ወይም የዓድዋ ተለዋጭ አድርጎ የ1888 ዓ.ም. ድልን መግለጽ በውጭ የታሪክ ጸሐፊያን ዘንድ ተደጋግሞ ያጋጥማል፡፡ የኢትዮጵያውያን የዓድዋ ድል  ‹‹የምኒልክ ድል›› እየተባለ መገለጽ የለበትም ብለን ማስተካከያ ለማድረግ ብንሞክር፣ ‹‹ዘይቤያዊ (ሥዕላዊ) አገላለጽን ለማረም የሚሞክሩት እነዚህ ሰዎች ታመው ነው ወይስ በጤናቸው!›› የሚል ትዝብት ውስጥ ነው የምንወድቀው፣ ከትዝብትም አልፎ መሳቂያ መሆን አለ፡፡ እናም ዘይቤያዊ አገላለጽን በዘይቤነት ዋጋው መረዳትና የታሪክ ሰዎችን በታሪክ ውስጥ በነበራቸው ጥንካሬና ህፀፅ መገምገም ለየቅል መሆናቸውን ማጤን ተገቢ ነው፡፡

ይህንን ማጤን አንድ ነገር ነው፡፡ ምኒልክ በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ በተጫወተው ሚና አከራከሪ ከመሆን አለማምለጡን (የሚወቀስበትም፣ የሚሞገስበትም ተግባር አለማጣቱን) ማጤን ደግሞ ሌላ ነገር ነው፡፡ እዚያ ክርክር ውስጥ አንገባም፡፡ ነገር ግን የ‹‹ዓድዋውን አስደማሚ ድላችንን ማወደስ›› እና ‹‹ምኒልክን ማወደስ›› አንድ ዓይነት ነገሮች አይደሉም፡፡ የዓድዋ ድልን ያገነነው የምኒልክ ስም ሳይሆን፣ በተገላቢጦሽ ለምኒልክ ስም በዓለም መግነን ምክንያት የሆነው ታሪከኛው የዓድዋ ድል ነው፡፡ ምኒልክ ከዓድዋ ድል በታች እንጂ፣ የዓድዋ ድል ከምኒልክ በታች አይውልም፡፡ የዓድዋ ዘመቻ ድል የጊዜው የአገር ልጆች አገር አቀፍ ተጋድሎ ውጤት ነው፡፡ የምኒልክ ንጉሠ ነገሥታዊ መሪነት የሚታየው በዚያ ዓውድ ውስጥ ነው፡፡

በዚያን ጊዜ ውስጥ በነበሩ አዝማቾችና ዘማቾች ውስጥ ከምኒልክ ጋር የማይጣጣሙ እንደነበሩ ሁሉ፣ በዛሬው ጊዜም ውስጥ የምኒልክ አወዳሽ ያልሆኑ፣ ግን የዓድዋ ድልን ድሌ ብለው የሚኮሩ ኢትዮጵያውያን አሉ፡፡ ምኒልክን አለማወደሳቸው የዓድዋ ድል የታሪክ ተጋሪነታቸውንና ኢትዮጵያዊነታቸውን አይቀንሰውም፣ በምኒልክ አምላኪነት ጥበት ውስጥ ያሉ ግለሰቦችና ቡድኖች ግን የምኒልክ አምላኪነት የተቀነሰበት የዓድዋ ድል አክባሪነት አይዋጥላቸውም፣ የምኒልክ አምላኪነት የጎደለበት ኢትዮጵያዊነት ለዓይናቸው አልሞላ ይላቸዋል፣ ለህሊና አክብሮታቸው ያንስባቸዋል፡፡ እንደ እነዚህ ያሉ ሰዎች የብዝኃ ኢትዮጵያውያንን የተባበረ እንቅስቃሴ ለሚያደፈርስ ሚና የተመቹ ናቸው፡፡

አሁን የ126ኛው የዓድዋ ድል የአዲስ አበባ አከባበር ወደ ታየበት መንገዳገድ እንምጣ፡፡ ሰላምና ዴሞክራሲን በአገራችን የመገንባት ተልዕኮ፣ በዓድዋ መንፈስ የሁላችንን ሆ ብሎ መነሳትንና በአንድ ላይ መንቀሳቀስን (ረዘም ላለ ጊዜም በዚሁ መንፈስ መፅናትን) ይጠይቃል፡፡ ያለ ጥርጥርም ይህን በማስተዋል፣ 126ኛው የዓድዋ ድል በዓል ጉልህ መነቃቂያችን እንዲሆን በማለት በኢትዮጵያ ደምቆ እንዲከበር ተፈልጎ ነበር፡፡ በአዲስ አበባ ከተማ የዓድዋ በዓል ሲከበር የቆየበት የምኒልክ አደባባይ ከዓድዋ ዘመቻ ጋር ታሪካዊ ዝምድና ቢኖረውም፣ በአደባባዩ የቆመው ሐውልት የአፄ ምኒልክን ሞገስ ያሰበ እንጂ በዓድዋ ተጋድሎ ላይ ያንፀባረቀውን የዕልፎች ጀግንነትና መስዋዕትነት ያሰበ አይደለም፡፡ ይህንን ባላሟላው (ፈረሰኛው ምኒልክ በተገሸረበት ሥፍራ) የዓድዋ ድልን ማክበር በምኒልክ ላይ ቅሬታ ላላቸው ሰዎች ለምኒልክ ከመስገድ ቁጥር ይሆንባቸዋል፡፡ በዓድዋዊ ሆደ ሰፊነት አንድ ላይ መትመም ለኢትዮጵያ መቀጠልና መገስገስ ወሳኝ መሆኑን የተረዳና በዓድዋዊ ሆደ ሰፊነት ውስጥ የሚያስብ ሰው ይህን ችግር ማጤን አይገደውም፡፡ ዓድዋን ድሌ ያሉ ሁሉ በልዩነቶች ሳይደናቀፉ ዓድዋን ሊያከብሩ የሚችሉበት ተስማሚና ተገቢ የመታሰቢያ ሥፍራ ላይ መገናኘት ይገባቸዋል፡፡

በምኒልክ ላይ ቅሬታ ያላቸው ኖሩም አልኖሩም፣ እስከ ዛሬ ዓድዋ ሲከበርበት የቆየው የምኒልክ አደባባይም ሆነ በዚህ ዓመት ለክብረ በዓሉ የተዳበለው ዓድዋ ድልድይ ለታላቁ ዓድዋ ድል አከባበር የማይመጥኑ ናቸው፡፡ ከምኒልክ አደባባይ ግርጌ በነበረው ኳስ ሜዳ ላይ አሁን እየተካሄደ ያለው ‹‹የዓድዋ ማዕከል›› ግንባታ ምን ዓይነት ይዘት እንዳለው ባላውቅም፣ ገናናው የዓድዋ ተጋድሎና ድል እንደ ገናናነቱ የተጋድሎ ይዘቱን በአግባቡ ያንፀባረቀ መታሰቢያና ብዙ የክብረ በዓል ተሳታፊን የሚያስተናግድ አደባባይ ያስፈልገዋል፡፡ አሁን የሚገነባው መታሰቢያ ይህንን የሚያሟላ ከሆነ እሰየው፡፡ ግንባታው የሚፈለግበትን ይዘት አሟልቶ ለመጪው ዓመት የዓድዋ በዓል ይደርስ ይሆን? ይደርስ ይሆናል፡፡ ያ ጊዜ ሲደርስ የዓድዋ ድል ክብረ  በዓል በአዲሱ ሥፍራ ሁሉን የዓድዋ ልጆች ያለ መሳቀቅ አገማሽሮ አይከበር ይሆን? በአሁኑ ዓመት አከባበር ላይ ከምኒልክ አደባባይ ወደ ዓድዋ ድልድልይ ሸርተት ለማለት ስለተሞከረ፣ የተለመደ ነገር ከቶም ሊቀየር እንደማይችል አድርገው ‹‹የክብረ በዓል ሥፍራ ለምን ተቀይሮ!›› ሲሉ የነበሩ አውጋዦችስ ፈረሰኛው ምኒልክን ሙጥኝ ብለው ይቀሩ ይሆን? የነገውን ለነገ እንተውው፡፡ ብንተወውም ግን፣ ስለዓድዋ መንፈስ እያወሩ ‹‹የተለመደ ቦታ መቀየር የለበትም›› የሚል ሙጥኝ ባይነት፣ ለዓድዋው ሰፊ ሱታፌ የማይጨነቅ ስስታም አቋም ስለመሆኑ ግን አንድና ሁለት የለውም፡፡

ከምኒልክ አደባባይ ግርጌ የሚገነባው ‹‹የዓድዋ ማዕከል” ለመጪው ዓመት የሚደርስ ቢሆን ብለን እናስብና ‹‹ለአንድ ዓመት መታገስ እንዴት ችግር ይሆናል?›› የሚል ጥያቄ አንስተን ብንመረምር ይጠቅመናል፡፡ ቢያንስ፣ ‹‹የዓድዋ ዘመቻንና ጦርነት የመራው ምኒልክ መሆኑን ታምናለህ አታምንም?›› በሚል ክርክር ለማፋጠጥና ለመርታት ለሚሞክሩ፣ ጉዳዩ በክርክር የመብለጥ ጉዳይ እንዳልሆነ ለመረዳት ያግዛቸዋል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡

የኦነግ ትግል ምን ዓይነት የፅንፈኛ አቋም ታሪክ እንደነበረው ላስተዋለ፣ ከዚያ ፅንፍ ተንሸራተው በፌዴራላዊት ኢትዮጵያ ውስጥ ኦሮሞ ከሌሎች ብሔር ብሔረሰቦች ጋር አብሮ መኖር ያዋጣዋል የሚል አስተሳሰብ የያዙ መገኘታቸው ትልቅ የፖለቲካ መሻሻል ነው፡፡ ኦነግ ነኝ የሚል ቡድን አባል ሆኖ፣ ኅብረ ብሔራዊ አመለካከት ያለው ብልፅግና ፓርቲ በሚመራው መንግሥት ውስጥ ለሁሉም የኢትዮጵያ ማኅበረሰቦች የሚሠራውን የባህል ሚኒስቴር የመምራት ኃላፊነት መቀበልም ፖለቲካዊ መሻሻልን የሚያሳይ ሌላ ፈርጅ ነው፡፡ ከዚያም አልፎ የዓድዋ አከባበርን በአዲስ አበባ ከተማ የማዘጋጀት ኃላፊነት ወስዶ ከፖለቲካ አኳያ ሁሉን አሳታፊ ሊያደርግ በሚችል አኳኋንና ሥፍራ ማዘጋጀት በመሠረቱ በጎ እንጂ ጥፋት አይደለም፡፡ በዓድዋ ድልድይ የተደረገው የአሁኑ ዓመት ዝግጅትም ሆነ፣ ከዚህ ቀደም በአብዮት አደባባይ የተካሄደው አከባበር ባህርያቸው ተመሳሳይ ነው፡፡ አከባበሩን ሁሉን አሳታፊ የማድረግ እንጂ ምኒልክን የመክዳት ወይም ታሪክን የመሻጠር ጉዳይ አይደለም፡፡ በብሔርተኝነት ውስጥ ያሉ ሰዎች ከፈረሰኛው ምኒልክ ዘወር ባለ ሥፍራ ሁሉን አሳታፊ በዓል ሊያዘጋጁ ሲሞክሩ፣ ለኢትዮጵያ አንድነት የማልሆነው የለም ባዮች ‹‹የኢትዮጵያ ታሪክ ተካደ! ሴራ ተሠራ!›› የሚል ጫጫታ ሲፈጥሩ ማየት (ኢትዮጵያን እንወዳለን ከማለት ጋር ጥበት ተጣብቆ ማየት) አስገራሚ ምፀት ነው፡፡

በኢትዮጵያችን ውስጥ በጋራ ታሪካችን ላይ ትርጉም ያለው መግባባት ቢፈጠርም፣ ምኒልክ በተለያዩ የታሪክ ጉዳዮች አከራካሪነቱ ይጠፋል ማለት አይደለም፡፡ ምኒልክን በተመለከተ ድፍርስ ስሜት የመኖሩ ነገርም የግለሰቦች ወይም የቅንጣት ቡድኖች ጉዳይ ብቻ አይደለም፣ ብዙ ሰዎችን የሚመለከት ነው፡፡ በአዲስ አበባ በፈረሰኛው ምኒልክ ሐውልት ዙሪያ ሲደርግ የቆየው የዓድዋ በዓል አከባበር የሚመለከተው የአዲስ አበባ ነዋሪዎችን ብቻ አይደለም፣ መላ ኢትዮጵያውያንንም የሚመለከት ነው፡፡ በዚያ ክብረ በዓል ላይ መሳተፍም በአካል የመገኘት ጉዳይ ብቻ አይደለም፡፡ በአካል ያልተገኘ የአዲስ አበባንም ሆነ የኢትዮጵያን ሰው ሁሉ ይመለከታል፡፡ ከዚህ ማዕዘን ቆመን በፈረሰኛው ምኒልክ ዙሪያ ዓድዋ መከበሩ ቅሬታ የሚፈነጥቅባቸው ምን ያህል እንደሚሆኑ በኢንተርኔት አማካይነት መረጃ ለማግኘት ብንሞክር ውጤቱ እጅግ ብዙ (ብሔርተኛ የሆኑና ያልሆኑን፣ ኦሮሞ የሆኑና ያልሆኑን ሁሉ የሚጨምር) እንደሚሆን አልጠራጠርም፡፡ እኔም ራሴን የማስገባው ከዚያ ቁጥር ውስጥ ነው፡፡ ምክንያቴ ምኒልክን የመጥላትና የመውደድ ጉዳይ ሳይሆን፣ ለገናናው ዓድዋ ድል መታሰቢያነት ፈረሰኛው ምኒልክ አለመመጠኑ ነው፡፡ ዓድዋ የሁሉን ተጋድሎ በአግባቡ የሚያንፀባርቅ ሐውልት ማግኘት ይገባዋል፡፡ ያንን በአግባቡ ማሟላት አቅቶን መከፋፈልና ቅሬታ ከእኛ ጋር ከዓመት ዓመት እንዲቀጥል መፍቀድ ትልቅ የፖለቲካ ጥፋት ነው፡፡ የምኒልክን ሐውልት ሙጥኝ ብሎ የዓድዋን ክብረ በዓል የአዛውንት አርበኞቻችንና የጥቂት ምኒልካውያን ተሳትፎ ሆኖ እንዲከሳ ማድረግና ማንንም ቅር በማያሰኝ መታሰቢያና ሥፍራ ላይ፣ ምኒልካውያን የሆኑም ምኒልካዊያን ያልሆኑም የኢትዮጵያ ልጆች የተገማሸሩበት በዓል ማዘጋጀት እጅግ ትልቅ ልዩነት አላቸው፡፡

‹‹ቀስ ብሎ ሊስተካከል የሚችል ነገር ሆኖ ሳለ፣ በዚህ የፈተና ጊዜ ለምን የማያስፈልግ ትንኮሳ ይደረጋል?›› የሚሉ ሰዎች ይኖራሉና የዚህን አስተሳሰብ ዕርባና እንመርምረው፡፡ በዓድዋ ክብረ በዓል ላይ ታሪክንና የክተት አዋጅን በማስታወስ ጊዜ፣ የአፄ ምኒልክን ስም መጥራት ይህን ያህል የሚያሳስብ አይደለም፡፡ በፈረሰኛው ምኒልክ ፊት ቆሞ ዓድዋን ማክበር ግን በእነ ቀጀላ መርዳሳ ‹ኦነግ›ም ላይ ሆነ በ‹ብልፅግና ፓርቲ› የኦሮሚያ ቅርንጫፍ ላይ የሚያሳድረው የፖለቲካ ተፅዕኖ ቀላል አይደለም፡፡ ዛሬ የምንገኝበት ወቅት፣ የእነ ቀጀላ መርዳሳን ‹ኦነግ›ም ሆነ ብልፅግና ፓርቲን የነፍጠኛ ተለጣፊ ወይም ሎሌ አድርገው ከኦሮሞ ለማቆራረጥ የሚሳሉና ሰበብ በመብራት እየፈለጉ አፍራሽ ፕሮፓጋንዳ የሚረጩ ፅንፈኞች በይፋም፣ ውስጥ ለውስጥም የሚሠሩበት ወቅት መሆኑን አንርሳ፡፡ በዚህ ሁኔታ ውስጥ የብልፅግና ኦሮሚያን የሚወክል ሰውም ሆነ መርዳሳ ቀጀላ ፈረሰኛው ምኒልክ ሐውልት ዘንድ ቆመው ስለዓድዋው ድላችን ንግግር ቢያደርጉ፣ የፅንፈኞቹን ሽርደዳና የኩነና ዘመቻ ሊያስፋፋ የሚችል ገበቴ ሙሉ ፍትፍት ከመስጠት የተናነሰ አይሆንም፡፡ በዚህ ዓይነት ፕሮፓጋንዳ የሚመጣው ክስረት ደግሞ የቀጀላ መርዳሳ ቡድንና የብልፅግና ፓርቲ የብቻ ጣጣ አይደለም፡፡ ለኢትዮጵያም የሚተርፍ ነው፡፡ ማለትም ከምኒልክ ሐውልት ጋር ከመጣበቅ ይልቅ ዓድዋን በአግባቡ የሚያንፀባርቅ መታሰቢያ ባለበት ሥፍራ የዓድዋን ድል ማክበር፣ ብሔርተኛን የማስደሰት/ምኒልክን የመካድ ነገር ሳይሆን፣ መላ ኢትዮጵያን በአግባቡ የማሰባሰብና የማስደሰት ጉዳይ ነው፡፡

እዚህ ላይ ተግባብተን ከሆነ፣ ከዚህ ቀደም አብዮት አደባባይ (መስቀል አደባባይ) በተደረገውም አከባበር ሆነ በዘንድሮው ከምኒልክ አደባባይ እስከ ዓድዋ ድልድይ በነበረው አከባበር ጥፋት የተሠራው፣ የቦታ ለውጥ ማድረግ ላይ ሳይሆን የሥፍራ ለውጡ የሽፍንፍን ሥራ መሆኑ ላይ ነው፡፡ ጉዳዩ ሽፍንፍንና መሳቀቅ የማያስፈልገው ትልቅ የፖለቲካ አስተዋይነት ጉዳይ ነው፡፡ በምኒልክ ሐውልት ዙሪያ ሁሉን አቀፍ በሆነ ተሳትፎ የዓድዋ ድልን ለማክበር መሞከር የተፈለገውን ሁሉን-አቀፍ ግዝፈት ለማሟላት የማያስችል ስለመሆኑ፣ እንደ ምንም ቢቃና እንኳ ፅንፈኛ የፖለቲካ ነጋዴዎች በከፋፋይ ፕሮፓጋንዳ የኅብረ ብሔራዊነቱን ሠፈር እንዲቦረቡሩ አመቻችቶ የመስጠት (ከፅንፈኛነት ሠፈር ወደ ኅብረ ብሔራዊነት እየሳቡ የማምጣቱንም ትግል የማዳከም) ጥፋት ስለመሆኑ ፊት ለፊት በፖለቲካ ፓርቲዎች ምክር ቤት ውስጥም ሆነ በተወካዮች ምክር ቤት ውስጥ ውይይት ቢደረግበት አስተዋይነት እንጂ ነውር አይሆንም ነበር፡፡ ሥጋቱና የቦታ ለውጥ ሐሳቡም የግድ ከብሔርተኛ በኩል መምጣት አይኖርበትም፡፡ የፖለቲካ ፓርቲ አባል ያልሆኑ ግን ፖለቲካዊ ጉዳቱን ያስተዋሉ ጋዜጠኞች/ምሁራን (ለተግባባ አገራዊ ርብርብ መጠናከር የሳሱ ልባሞች) የውይይት አጀንዳ አድርገው በመገናኛ ብዙኃን ላይ ሊያቀርቡትም ይችሉ ነበር፡፡ የሐሳብ ልውውጡ ሰፋ ያለ መግባባት ከፈጠረ ለአዛውንቶቹ አርበኞቻችን ዱብ ዕዳ አይሆንባቸውም ነበር፡፡ አከባበሩን ከሁለት ሥፍራዎች ጋር የተያያዘ የማድረግ ጊዜያዊ መፍትሔም የሚሽሟጠጥ ባልሆነ ነበር፡፡ ቢያንስ ‹‹በኢትዮጵያ አፍቃሪነት›› ስም የሚነግዱ ጠባቦች ግርግር ለመፍጠር ድፍረት አያገኙም ነበር፡፡

በጊዜው የወረደው የትችት ናዳ፣ በሽፍንፍን አካሄድና አወሳሰኑ ላይ ቢሆን ኖሮ ጎሽ ባልን ነበር፡፡ ከታሪክ ውስጥ የብሔሬ ጀግና ብሎ መምረጥንና ሌላውን መተውን (በተለይ የፌዴራል ሥልጣንን በወከለ ንግግር ላይ) ልክ አይሆንም ብሎ መተቸትም አግባብ ነበር፡፡ የተካሄደው ትችት ኃላፊነት ይሰማቸዋል በሚባሉ ሰዎች ዘንድ ሳይቀር ግን፣ ከገንቢነቱ ይልቅ አፍራሽነቱ ያመዘነ ነበር፡፡ በብልፅግና ሰዎችም ላይ ሆነ በእነ ቀጀላ መርዳሳ ላይ የነበረውን አጣብቂኝ (ከምኒልክ አምላኪ ፅንፈኞችም፣ ከምኒልክ ጠል ፅንፈኞችም በኩልም የሚያዋክባቸውን ሁለት ዓይነት ውግዘት) የተረዳ ሰው በአከባበሩ ላይ የታየውን መለስተኛ የሥፍራ ለውጥ ‹‹አመልን በጉያ ያለ ማድረግ››/‹‹የሴረኛነት›› ጉዳይ አድርጎ አይተረጉመውም፡፡ ከዚህም የባሰም ተብሏል፡፡ ፅንፈኞች በፊት በፊት የዓድዋ ታሪክ የእኛ አይደለም ይሉ እንዳልነበር፣ አሁን አሁን ታሪክ ነጠቃ ጀምረዋል ያለ ንድፈ ሐሳብ መሰል፣ ግን አባ ውቃው የሆነ ድምዳሜ የመንግሥት ባልሆነ የቴሌቪዥን መደበኛ አገልግሎት ላይ ሲወረወር ሰምተናል፡፡ የመገናኛ ብዙኃን ጋዜጠኞች ከማንም ይበልጥ የሚተነፍሷት ነገር ሚሊዮኖች ጋ እንደምትደርስ አውቀው ሊጥና የተሳሳተ ነገር ከአንደበታቸው/ከብዕራቸው እንዳይወጣ እጅግ መጠንቀቅ ይገባቸዋል፡፡ የመገናኛ ብዙኃን ኃላፊዎችና የፕሮግራም መሪዎች ይህንን መከታተል በሚያስችል ሥርዓት ውስጥ መንቀሳቀሳቸውም የሙያ ግድ ነው፡፡ አንዳንድ የግል ቴሌቪዥን መሰናዶዎች ግን፣ ይህንን ኃላፊነት ይቅርና የድምፅ ሳቢ አለመሆንና የአነጋገር ችሎታ ማነስ አድማጭ/ተመልካችን አባራሪ መሆኑን ማወቃቸው እንኳ ያጠራጥራል፡፡

ቴሌቪዥኖችና ሬዲዮኖች ዘንድ ዛሬ ዛሬ የምናየው የአገር ወዳድነት ስሜት መልካም የሚባል ነው፡፡ ነገር ግን በኢትዮጵያ ሁነኛና ወቅታዊ ችግሮች ላይ ፓርቲዎችንና ሊቆችን አገናኝቶ የአንዱን አተያይና ትንታኔ ከሌላው ጋር እንዲገናዘብ/እንዲፈተግ፣ ከዚህም ሒደት ንጥር ውጤት እንዲፈለቀቅ በማድረግ ከሁሉም በላይ ሕዝብን አትራፊ የማድረግ ተግባር በአገራችን የሌለ ያህል ነው፡፡ አንዳንዶች ዘንድ የህልም ያህል የሚሞካከር ቢሆንም፣ በአወያይነት/በጠያቂነት ዘንድ ያለ የትባት ማነስና በጉዳዮች ላይ ነገሮችን ለመበርበር የሚያበቃ ዕውቀት አለመጨበጥ ትልቅ ችግር ሆኖ ሙከራውን መና ያስቀረዋል (ለምሳሌ ጥር 27 ቀን 2014 ዓ.ም. በአሀዱ ተላልፎ የነበረ ቃለ መጠይቅ)፡፡ ከዚህ ዓይነት ሙከራዎች ውጪ በመንግሥትም ሆነ በግል ሬዲዮኖችና ቴሌቪዥኖች ዘንድ የምናገኛቸው ቃለ መጠይቆች በሚዲያው (በጠያቂው) እና በተጠያቂዎቹ መሀል የዝንባሌ መፈላለግ ወይም መቀራረብ ያለባቸው የሚመስሉ ናቸው፡፡ በቀላል አነጋገር ጠያቂዎቹ በዚህ ጉዳይ ላይ በደንብ አድርገው ይደስኩሩልኝ በሚል መንፈስ የሚሠሩ መሳዮች ናቸው፡፡ በተረፈ ያለ ፖለቲካ ዝንባሌና ያለ ብሔር ወገናዊነት ልዩነት ሁላችንን የሚያገለግሉ ብሎ ሕዝብ የሚያምናቸውና የሚያከብራቸው መገናኛ ብዙኃን የሉም ማለት ይቻላል፡፡ በተወሰነ ደረጃ በሕዝብና በኢሳት መሀል የምናየው፣ ከአገር ወዳድነት በመለስ ብሶትን ሰምቶ ከማሰማት ቀጭን ክር ያለፈ አይደለም፡፡ ኢሳት ላይ ካየናት ብርቅዬ ክር ውጪ ሁሉም ቴሌቪዥኖች ኢሳትን ጨምሮ ፓርቲያዊ ወዘና ወይም አጋዳይነት ያላቸው ናቸው፡፡ ከአጋዳይነት ባለፈ ማዕከላዊ ኮሚቴ ምናምን የሚባለው መዋቅር ከመጉደሉ በቀር፣ ሚዲያ ራሱ የፓርቲ ዓይነት ፀባይ ይዞም እናገኛለን፡፡ በአገር ወዳድነት አገርን መጥቀምን ፓርቲያዊ ካለመሆን ጋር አዛምዶ የሚሠራ አለ ቢባል ሸገር ሬዲዮ ይመስለኛል፡፡ እሱንም ለመጥቀስ የበቃሁት በቅዳሜ የ‹‹ጨዋታ›› እና በእሑድ ‹‹ካፌ›› ዝግጅቶቹ ላይ ተመሥርቼ ነው፡፡ ሁለት ፕሮግራሞች ላይ ተመርኩዤ ‹‹ኢፓርቲያዊ›› ለማለት የተደፋፈርኩትም ሸገር አንገብጋቢ ሆነው ለሚያገኛቸው የአገር ጉዳዮች መላ ሲያፈላልግ ወደ ማናቸውም ፓርቲዎች ገልመጥ አለማለቱን፣ ባለሙያዎች በማወያየት ላይ ማተኮሩንና ከእነዚህ ባለሙያዎችም ብዙዎቹ ለዚህ፣ ለዚያ ፓርቲ የቀረቡ ናቸው ለማለት የማይመቹ መሆናቸውን ይዤ ነው፡፡

በእርግጥ ሙያዊ ማብራሪያና መፍትሔ ለሚሹ ጉዳዮች አግባብነት ያላቸውን የሙያ በሳሎች እያቀረቡ ማናገር መንግሥትንም፣ ፓርቲዎችንም፣ ሕዝብንም የሚጠቅም አንድ ነገር ነው፡፡ ስብርባሪ ቡድኖች ዘንድ ሳይናውዙ፣ ትልልቅ የሚባሉት ፓርቲዎችና መንግሥት ሕዝብን በሚፈይድ መሰናዶ ቋታቸው ምን ያህል ከጊዜ ጊዜ ትኩስና ሙሉ ሆኖ እንደሚገኝ መፈተሽና ማነፃፀር ያንኑ ያህል አገርን መጥቀም ነው፡፡ ከተወያይ ፓርቲዎች የሚገኙ ምላሾች እርስ በርስና ከምሁራን አስተያየቶች ጋር ተነካክተው የሚያስገኙት ሦስተኛ ውጤት ፋይዳው ቀላል አይደለም፡፡ የተፈተገ ነገር እንዲገኝ ሲባል፣ ለፓርቲዎች አስቀድሞ ጥያቄዎችን ያሳወቀ የውይይት መሰናዶ (በሬዲዮና በቴሌቪዥን ማግኘት) ለኢትዮጵያ ሕዝብ ዛሬ ብርቅ ሊሆንበትም አይገባም፡፡ ከተሬ ልብታ ጋር ረድፍ ገብቶ ገች ገች የማይል፣ ተሬዎችን ያለፈ መስሎትም ከአየር እየቧጠጠ ሴራና ሚስጥር የማይፈለስፍ፣ ግን የፖለቲካ-ኢኮኖሚ ነገረ ሥራዎችንና ትንፋጎችን እየተከታተለ የሚያበራይ፣ በፖለቲካ ቡድኖች ዘንድ ምን ያህል ደፈጣዎች፣ የሾኬ ጠመዳዎችና መጠባበቆች እንዳሉ በማንበብም የሕዝብ አዕምሮና ጥቅሞች የመጠላለፍ መጫወቻ እንዳይሆኑ ፈጥኖ የሚያነቃ ሚዲያ፣ የኢትዮጵያ ኅብረተሰብ የማግኘቱ ነገር ገና ገና ብዙ ፀሎት የሚያስፈልገው ይመስላል፡፡

ይህ የምር ስሜቴ ነው፡፡ ምክንያቱም ነባራዊነትን፣ እቅጩነትን፣ ሚዛናዊነትን፣ እውነት ፈላጊነትንና ሕዝብ/አገር አገልጋይነትን መገናኛ ብዙኃን አሳልጠው የመሥራታቸው ጉዳይ እንደ አዲስ መታነፅን የሚጠይቅ ነው፡፡ የአንዱ መርሆ መፍካት የሌሎቹን ሰበዞች አስተዋጽኦ ይፈልጋል፡፡ እቅጩ መረጃዎች ሳይዙ እውነትን ፍለጋ የለም፡፡ የብሶተኞችን አቤቱታና አቤቱታ የቀረበባቸውን አካላት ማስተባበያ ያለ አድልኦና ያለ ስሜታዊነት ሳይበረብሩ እቅጩ መረጃዎችን ማግኘትና አገርን ማገልገል አይኖርም፡፡ እነዚህን ሰበዞች ያሳሉ ሚዲያዎች ሊያብቡ የሚችሉት እንዲህ ያለው ባህርይ የፍሬያማ ሚዲያ መለኪያ መሆን ሲጀምርና መርሀዊ ሥራን በአግባቡ መወጣት ለጋዜጠኞች መመስገኛና ማደጊያ እንጂ፣ ሰበብ ተፈልጎ መባረሪያ አለመሆኑን የሚያግዝ ሥርዓት ሲፈጠር ነው፡፡ በሌላ አነጋገር የጋዜጠኛ እያንዳንዷ ሥራ (ቃለ መጠይቅ፣ ውይይት፣ ፈልፋይ ዘገባ፣ ወዘተ.) ተበጥራ እየተገመገመች ከጊዜ ጊዜ የጥራት ዕድገት ማሳየት ለጋዜጠኛ መቆያውና መሞገሻው፣ ከቅቤ ጠባሽነትና/ከአባ ውቃውነት አለማለፍ ደግሞ መቅለያውና መሰናበቻው ሲሆን ነው፡፡

 የተመረጡ ነጥቦችን ላስቀምጥና ይህንን ክፍል ላጠናቅቅ፡፡

  • ታሪክን በማውሳት ላይ የምኒልክንም ሆነ የማንኛውንም አፄ ስም መጥራት አስፈላጊ በሆነበት ሥፍራ ምን ይሉኝ ሳይሉ ለመናገር መቻል ራስን ከግብዝነት ነፃ የማውጣት ጉዳይ ነው፡፡
  • ታላቁን የዓድዋ በዓል በስም ያልታወቁ ግን ወራሪዎችን ያራዱ ዕልፍ አዕላፍ ጀግኖችንና መስዋዕታትን ባገዘፈና የታወቁ ጀግኖችንና መሪዎችን ባንፀባረቀ መታሰቢያ ዘንድ አበባ እያስቀመጡ ለማክበር መቻል የታሪክ ኃላፊነትን በአግባቡ መወጣት ነው፡፡
  • የዳግማዊ ምኒልክንም ሆነ የሌሎች አፄዎችንና የአካባቢ ገዥዎችን ህፀፅና ጥንካሬ፣ በኖሩበት ዘመን የአስተዋይነት ዓውድ ልክ ለመገንዘብ መጣጣር፣ ሚዛናዊ የታሪክ አረዳድን ለመቆናጠጥ የመጣጣር ጉዳይ ነው፡፡

የመጪው ዘመን ጉዟችን ወደ እዚህ ዓይነቱ የአዕምሮ ነፃነት የሚያመራ እንደሚሆን ተስፋ አደርጋለሁ፡፡

ለ) የሩሲያና የዩክሬይን ጦርነት ለአፍሪካ ትምህርታዊነቱ

የዓድዋ ሆደ ሰፊ መንፈስ ለኢትዮጵያ የውስጥ ጣጣችን ብቻ ሳይሆን፣ ለአፍሪካ ቀንድ ግቢያችንም ሆነ ለአኅጉራችን በሞላ አስተማሪነት አለው፡፡ ለውጭ ኃይል ጭራን እያወነወኑ ዘመድ ጎረቤትን መተንኮስ ይበጃል? የተነኮሰኝን ልቅጣ ከማለትም ሆነ እየተዋጉ ከመደማማት የሚያተርፈው ማነው? ተዋጊዎቹ ዘመዳሞች ወይስ ሌሎች? የዩክሬይንና የሩሲያ ቀውስ ለዚህ ሁሉ መልስ ይሰጣል፡፡ ዩክሬይን ከሩሲያ ጋር የተማመነ ወዳጅነት ለማዳበር ከምዕራብ አገሮች ጋር መቆራረጥ እንደማያስፈልጋት ሁሉ፣ ከምዕራብ አገሮች ጋር ስኬታማ ወዳጅነት ለማዳበር ከሩሲያ ጋር ያላትን ዝምድናና ባልንጀርነት መሰዋት አይጠበቅባትም፡፡ አስተዋይነት ካለ ሁለቱንም አቻችሎ ማስኬድ ይቻላል፡፡ የዩክሬይንን ደኅንነት የሚያስጠብቀውም ከሩሲያ ጋር ተቋስሎ ወደ ኔቶ ጎራ መሸሽ ሳይሆን፣ ከሁለቱም ጋር ጤናማ ወዳጅነት መገንባትና በዚህ ውስጥ ታሪካዊ ዘመድን በቅጡ ማወቅ ነው፡፡ እዚህ ላይ በተፈጠረ ጥፋት ምክንያት የዩክሬይን መንግሥት ከሩሲያ ጋር የተያያዘ ታሪክ ያላትን ክሪሚያን አስወስዷል፣ በምሥራቅ በኩል የመነጠል እንቅስቃሴ እንዲቀሰቀስ የረዱ ሁኔታዎችን ፈጥሯል፣ የአሁኑን አውዳሚ ወረራ በዩክሬይን ላይ ጠርቷል፡፡

የአውሮፓ አውራዎች ጀርመንና ፈረንሣይ ከልዕለ ኃያል መሪያቸው ከአሜሪካ የማፈንገጥ ድፍረት ያሳዩት፣ የኢራቁን ሳዳም ሁሴን ለመጣል በታቀደ ዘመቻ ጊዜ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ ከአፍሪካ ጋር አጋርነት ፈላጊዎች የተበራከቱትም ከዚያ በኋላ ነበር፡፡ ከዚያ ቀጥሎ ምዕራባዊው ጎራ ጉልህ እገጭ እጓ የገጠመው በዶናልድ ትራምፕ ጊዜ ነበር፡፡ ጃፓንና ደቡብ ኮሪያም ከቻይናና ከደቡብ ምሥራቅ እስያ (ASEAN) አገሮች ጋር ተራክቧቸውን በደንብ ተንከባክበው መያዝ እንዳለባቸው ልብ ያሉት (አሜሪካ ላይ የመንተራስ ጊዜ ማለቁን የተረዱት)፣ ጀርመንና ፈረንሣይም ለአሜሪካ ሳይቅለሰለሱ እንደ አውሮፓዊ ጎራ አንገታቸውን ቀና ቀና ያደረጉት ያኔ ነበር፡፡ ትራምፕ ሄዶ የተተካው ጆ ባይደን በአሜሪካና በአውሮፓ መሀል ትራምፕ የፈጠረውን ንቃቃት ለመጠገን፣ ቻይናንና ሩሲያን ለምዕራብ ደኅንነትና ጥቅም አደገኛ ሥጋት አድርጎ ማቅረብን ቢጠቀምም፣ ዕይታው ቦዞ የሚበለጥ አልተገኘም፡፡ ከቃላዊ ‹‹መግባባት›› በቀር ከቻይናና ከሩሲያ ጋር ያላቸውን የኢኮኖሚ ተራክቦ ለማቁሰል አንዳቸውም አልፈቀዱም፡፡ የጆ ባይደን አሜሪካ በመስከረም 2014 ዓ.ም. ውስጥ ቻይናን ለመመከት ይመስላል አውስትራሊያ፣ ብሪትን (ዩኬ) እና አሜሪካ የተቀናበሩበት ‹‹AUKUS›› የሚባል የቢቸግር ሽርክና መፍጠሯ፣ ሽርክናዋን የፈጠረችውም አውስትራሊያ ከፈረንሣይ ባህር ሰርጓጅ የኑኩሌር መርከብ ለመግዛት የነበራትን ስምምነት አፋርሳና ፈረንሣይን አስቆጥታ መሆኑ ንቃቃት የመጠገን ሙከራው እንዳልሠራ የጠቆመ ነበር፡፡

ዩክሬይንን በኔቶ አባልነት የመቀበል ፍላጎት መሞቁ ሩሲያን አስቆጥቶ፣ ሩሲያ ዘመድ-ጎረቤቷን በየካቲት አጋማሽ 2014 ዓ.ም. መውረሯ ነገሮችን ቀየረና አሜሪካና አውሮፓ ወደ ድሮ ጎራቸው የተመለሱት፣ የኔቶም ዕርባና የታደሰ መሰለ፡፡ እነ ፈረንሣይ ጦርነት ደጃቸው መፈንዳቱ እነሱንም ሊያከስል የሚችል አደጋ እንዳለው የምር አምነው ከነበረና የጦርነቱ መቋረጥ ቁርጠኛ ፍላጎታቸው ከነበረ፣ የዩክሬይንን ወደ ኔቶ የመግባት ፍላጎት ውድቅ አድርገው ሩሲያን እስከ ማብረድ መሄድ ነበረባቸው፡፡ ‹‹ጥቃትሽ ጥቃቴ፣ ዘመቻሽ ዘመቻዬ›› ባይ ኪዳን ያለውን ወታደራዊ ጎራ በተቀናቃኝነት የሚታይ አገር በራፍ ድረስ ማስፋት የመብት ጉዳይ ሳይሆን ሙልጭ ያለ ነገረኝነት ነው፡፡ ዩክሬይንን የኔቶ አባል ለማድረግ የፈለጉት ለእነሱ ሥርዓት ከሩሲያ በተሻለ ቅርብ ሆና ነው አይባል ነገር ሩሲያ የምትታማበትን በዴሞክራሲ ማንከስን፣ በሙስናና በመብት ጥሰት መጉደፍን ዩክሬይንም ትታማበታለች፡፡ ትንሿን ዩክሬይን ከትልቋ ሩሲያ ጥቃት  ለመጠበቅ አስበው ነው አይባል ነገር፣ ሩሲያ እነሱ የማያደርጉትን አላደረገም፡፡ አሜሪካም ሆነች አውሮፓውያኑ ኃያላን፣ እስያና አፍሪካ ድረስ እየተወረወሩ ቀውስ የሚያባብሱ ደብረ በጥብጦች መሆናቸው ይታወቃልና ሩሲያን ለመኮነን የሚያበቃ የህሊና ንፅህና የላቸውም፡፡

ነገረኛነታቸውን የሚያጋልጥ መሰል ታሪክም አለ፡፡ እ.ኤ.አ. በ1962 በጆን ኤፍ ኬኔዲ ፕሬዚዳንትነት ጊዜ ሶቪዬት ኅብረት ኩባ ውስጥ የረዥም ርቀት ሚሳይል መትከሏን የሚያመለክት የሰማይ ላይ የፎቶ መረጃ ይዛ አሜሪካ ጦርነት ለመክፈት አገንግና ነበር፡፡ ጦርነቱ መቅረት የቻለው ሶቪዬቶች ሚሳይሉን ሊያነሱ፣ አሜሪካም ኩባን ላትወር ስምምነት ተደርሶ ነበር፡፡ ያኔ አሜሪካ ደጇ ላይ ሚሳይል መጠመዱን የኩባ መብት ብላ እንዳልተወችውና ከጦርነት ፍለጋ እንደቆጠረችው ሁሉ፣ ኔቶ እነ ፖላንድ ላይ ሚሳይል መጥመዱ ሳያንስ የኔቶን አጥር ሩሲያ ድንበር ድረስ እስከ ማምጣት መሄድ እንዴት በዝምታ ይታያል ተብሎ ይታሰባል? ነገር ፈላጊዎቹ በተቀዳሚነት ኔቶዎች መሆናቸው አከራካሪ አይደለም፡፡ ሩሲያን ለኔቶ ነገረኛነት ያጋለጣት ግን፣ ከቀድሞ የሶቪዬት ኅብረት ዘመዶቿ ጋር ያላትን ግንኙነት ጤናማና ቤተሰባዊ አድርጋ አለመገንባቷ ነበር፡፡ ሩሲያ ከዩክሬይን ጋር በግዛት ቡጨቃ የገባቸው ቅራኔ ለዕርቅ የሚመች አልነበረም፡፡ የዩክሬይን መንግሥት በኔቶ አለኝታነት ላይ መተማመንም እንዲሁ ከቅዠታምነት ያልተናነሰ ነበር፡፡ የሩሲያ ወረራ በዩክሬይን ላይ ከተከፈተ በኋላ ግን ቅዠቱም፣ ሞኝነቱም፣ ብልጠቱም፣ አትራፊነቱም የት የት እንዳለ ወለል ብሎ ታየ፡፡

የኔቶ ኃይሎች የሩሲያና የዩክሬይን ጦርነት ከተከፈተ በኋላ ከቀጥተኛ ጦርነት በመለስ ልዩ ልዩ ግንኙነቶችን አቋርጦ ሩሲያን ከዓለም በማግለል እስከ መቅጣት ያከረሩት፣ ለአንዳንዶች እንደሚመስላቸው የኑክሌር ጦርነት እንዳይነሳ ወይም ለዓለም ሰላም በማሰብ አይደለም፡፡ የሩሲያ የኃያልነት ጉልበት መሟሟት ለአሜሪካም ሆነ ለአውሮፓ ኃያላን የጋራ ጥቅማቸው ነው፡፡ ከዚህ አኳያ የዩክሬይንን መወረር ‹‹ቢናደዱበትም››፣ ‹‹አይጠሉትም››፡፡ ‹‹ሩሲያ የቀድሞ ሶቪዬት ኅብረትን የመመለስ ፍላጎት አላት›› የሚለው ቅብጥርጥር ተውኔት ነው፡፡ የሩሲያን አቅም የማሟሟት ውጤት ላይ ለመድረስ ጦር መሣሪያ የሚያንደቀድቅ ውጊያ ውስጥ መግባት አያስፈልጋቸውም፡፡ ለዚያ ተግባር ዩክሬይን የመስዋዕት በግ ሆና ታገለግላቸዋለች፡፡ ዩክሬይንን የመስዋዕት በግ በማድረግም ጉዞ ውስጥ በመሣሪያና በገንዘብ ዩክሬይንን ‹‹እያገዙ›› እና ቅጥረኛ ወታደሮች እያሰረጉ ጦርንቱን በማራዘም ውጤቱ ሩሲያን ያሰለሰለ እንዲሆን የሚችሉትን ሁሉ ይጥራሉ፡፡ ሩሲያ ዩክሬይንን ፍርስራሽ በፍርስራሽ አድርጋ የኔቶ አባልነትን ዕምቢኝ ያለ አሻንጉሊት መንግሥት ብትጎልት እንኳ፣ የዩክሬይን ‹‹ሕጋዊ መንግሥት እስካልተመለሰ ድረስ…›› በሚል ‹‹አሳቢነት›› ሩሲያን ከዓለም ሕይወት የመነጠል ጦርነታቸውን ይገፉበታል፡፡ ያ ሁሉ ሲሆን ዩክሬይን መንደድ መጤሷ ቢቀጥል ይህን ያህል ጉዳያቸው አይደለም፡፡ ስደተኛ መቀበል፣ በዩክሬይን ውስጥ ለተቸገሩ ደራሽ ዕርዳታ መስጠት፣ ወዘተ ‹‹የሩኅሩኅነታቸው›› ማረጋገጫ ሆኖ ይሠራላቸዋል፡፡ ሩሲያ ወላልቃ ምናልባትም ተጨማሪ መፈረካከስ ደርሶባት አስፈሪ ልዕለ ኃያል ሆና መታየት የማትችልበት ሽንፈት ውስጥ ከገባች፣ በፍርስራሽ እስከ መዋጥ የነኮተችው ‹‹በጊቱ›› ዩክሬይን በዕርዳታና በድጎማ ‹‹ተቀማጥላ›› የኔቶ አባል መሆንን አታጣም፡፡ ያኔ ዩክሬይን ብትባንን ዋጋ የለውም፡፡ ሁለቱንም ዘመዳም አገሮች የሚያወራርደውን ይህንን የኔቶ ኃያላን ሥሌት ለመረዳት ሩሲያና ዩክሬይን ቦነው እስኪጠፉ መጠበቅ አያሻቸውም፡፡ አሁን ያሉበት እውነታ ቅዠትን፣ እልህን፣ ቁጣን በረጋግዶ ቂል መሆን እንደሌለባቸው እየነገራቸው ነው፡፡ ሁለቱም አገሮች ይህንን ያስተዋለና ያዳመጠ አዕምሮ ካላቸው አሁኑኑ ‹‹የምን የኔቶ አባልነት ብሎ ነገር!›› ተባብለው በጊዜ ሒደት ክሪሚያን ወደ መመለስ የሚወስድ እውነተኛ ዕርቅና ቤተሰባዊ ግንኙነት ውስጥ መግባት ይጠበቅባቸዋል፡፡ 

ይህ ተስኗቸው ኔቶዎች በዩክሬይን መስዋዕትነት አማካይነት ኃያልነቷ የተደቆሰ ሩሲያ ላይ ለመድረስ የሚያካሂዱት ብልጠት የሚያስገኘው ውጤት እነሱ ያሰቡት ብቻ ላይሆን ይችላል፡፡ ሩሲያ ‹‹ማን ሲጠፋ ማን ቆሞ ሊስቅ!›› በሚል እልህ ናላዋን ብትስት፣ ጦርነቱ መላ አውሮፓን እስከ ማቃጠል ሊከፋ ይችላል፡፡ ያኔ ጦርነቱ ከኑክሌር በመለስ ሆኖ ለመትረፍ ዕድል ከተገኘ፣ እነ ጀርመንን የሚያስቆጭ ቁማር ውስጥ መግባታቸውን ያጤኑታል፡፡ የአውሮፓ ሕዝብም ‹‹ጦርነት/ወረራ ይቁም!›› ከማለት ባሻገር ‹‹የኔቶ ተስፋፊነትም ይቁም!›› ብሎ መጮህ እንደነበረበት የጦርነቱን ጥፋት ከቀመሰው በኋላ ይረዳል፡፡ በዚያ ሒደት ውስጥ አሜሪካ ጉልበት ቆጥባ የእነ ጀርመንን ልዕለ ኃያላዊ መንጠራራት የማስተንፈስ ብልጠት ታመጣ ይሆናል፡፡ የዚያ ዓይነት ብልጠት በበኩሉ እነ ጀርመንን አሸፍቶ ከሩሲያ እስከ መታረቅና የጎራ ሽርክናን እስከ መቀየር ይወስዳቸው ይሆናል፡፡ ይህ ምናልባታዊ ሁነት ተከሰተም ቀረ፣ እስካሁን ድረስ የአውሮፓ ሕዝብ ከኔቶ ጋር በጭፍን አብሮ መክነፉ ከዩክሬይን እስከ አውሮፓ ድረስ ግጥጥ ብሎ የወጣው ዘረኛ መድልኦ የጠነነበት የስደተኛ አቀባበል ላይ እንኳ ይህ ነው የሚባል ውግዘት አለማካሄዱ፣ ምን ያህል ለሰው ልጅ መቆርቆርን ያከረከሰ ማሽቆልቆል ውስጥ እንደገባ የሚጠቁም ነው፡፡

ጦርነቱ ከእነ ዩክሬይን ተሻግሮ አውሮፓን ባይለመጥጥ እንኳ፣ ሩሲያን በፋይናንስና በኢኮኖሚ ቀውስ አይሆኑ እንድትሆን የተከፈተው ሁለገብ አፈና፣ ጉዳቱ በማን ይብስ የማለት ነገር ካልሆነ በቀር ምዕራባውያኑን ሁሉ መደቋቆሱ አይቀርም፡፡ የባሰ ይባስበት ጥቃቱ የሩሲያን ወገብ ሰባብሮ ተሸናፊ ካደረገ በዓለም ልዕለ ኃያላዊ ሚዛን ላይ የሚፈጥረው መዛባት ቀላል አይሆንም፡፡ የአሜሪካ አውሮፓ ኃያልነት አብጦ ቻይና ሁነኛ የኃያልነት አጋሯን አጣች ማለት ነው፡፡ ያ ደግሞ  ደቃቆችን ማኩረፊያ እስከ ማጣት ሊያደርሳቸው ይችላል፡፡ ቻይና ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ያመጣችው ልበ ሙሉነት ሊረግብና እንደማፈግፈግ ሊል ይችልም ይሆናል፡፡ ያኔ ቻይናም ጅብ ከሄደ በኋላ ፀፀተኛ ትምህርት ማግኘቷ አይቀርም፡፡ ያኔ ብቅ የሚለው ትምህርትም፣ ፊት መወሰድ የነበረበት ዕርምጃ ዩክሬይንን መውረር ሳይሆን ሩሲያና ቻይና አንድ ላይ ቆመው ‹‹ኔቶዎች መስፋፋታችሁን ካላቆማችሁ የዓለም ሰላም አደጋ ውስጥ ይወድቃል›› በሚል ማስጠንቀቂያ ከኔቶ ጋር ተፋጥጦ፣ የዓለም ኅብረተሰብን ማባነን መሆን ነበረበት የሚል ይመስለኛል፡፡ በእርግጥም ይህንን ፍጥጫ ደፍረውት ቢሆን ኖሮ፣ የዩክሬይን የኔቶ አባል የመሆን አጀንዳ የመታጠፉ ዕድል በሰፋ ነበር፡፡ ነገሮች ከተበላሹ በኋላ የዚህ ዓይነቱ የቁጭት ትምህርት ቢገኝ ምን ሊፈይድ? አሁንም ሌላው ቢቀር ሩሲያና ዩክሬይን የገቡበትን ወጥመድ ተረድተው ጦርነት እንዲያቆሙና እንዲታረቁ ቻይና ብትረዳ ይሻላታል፡፡

የአንዱ ወይ የሌላው ኃያል/ልዕለ ኃያል አረጥራጭ ሆኖ ከጎረቤት/ከአዝማድ ጋር ጦርነት ውስጥ መግባት ምን ያህል ሁለቱንም ወገኖች እንደሚያደቅ ኢትዮጵያውያን በውስጥ ቀውሳችን ዓይተነዋል፡፡ የሕወሓት ጦረኛ አበጋዞች ቁራጭ አገር ፈጥረው ዙፋን ላይ የመቀመጥ ቅቤን ለመጠጣት ሲሉ በከፈቱት ጦርነት፣ ምን ያህል የትግራይን ሕዝብና ኢትዮጵያን እንዳደሙ ለመረዳት ዛሬ ተራኪ አያስፈልገንም፡፡ የዩክሬይንና የሩሲያ ጦርነትም ሁለቱንም እንደሚያማቅቅ ገና ከወዲሁ ለመረዳት ኢትዮጵያውያን እንደማይቸገሩ ይታመናል፡፡ ሌሎች አፍሪካውያን ወገኖቻችንም መማር አለባቸው፡፡ ትምህርቱ ግን ከዝምታ አልፎ የደቡብ አፍሪካን ጥረት አኅጉራዊ እስከ ማድረግ ማደግ ያለበት ይመስለኛል፡፡ ኔቶዎች ዩክሬይንን የመስዋዕት በግ አድርጎ ሩሲያን በወራሪነት ከዓለም ነጥሎ የማወራረድ ግብግባቸው ከተሳካ፣ የአፍሪካ አገሮች ወደ ፊት ምን ያህል እግር ብረት እንደሚጠብቃቸው በደንብ ይታየኛል፡፡ ይህ እንዳይሆን ዩክሬይንና ሩሲያ ልብ ገዝተው በዕርቅ በኩል ከሞት ድግሱ እንዲወጡ መጣጣር ያስፈልጋል፡፡ በበኩሌ ይህ እንዲሆን ፀሎቴ ነው፡፡ ይህ ባይሆን ሩሲያን ለማወላለቅ ምዕራባውያን የተያያዙት ከማንኛውም ድንበር ተሻጋሪ ንግድና ሥራ ከፈታ የመከርቸም አድማው፣ በኑሮ ውድነትና በኢኮኖሚ ቀውስ ጠንቁ ዓለምን አስመርሮ የዓለም ሕዝብ ከዳር ዳር የኔቶን የመስፋፋት ትንኮሳ አውግዞ የጦርነቱን መቆም እንዲያግዝ እመኛለሁ፡፡ የአፍሪካ ኅብረት ቢያንስ ‹‹ለዓለም ሰላም ሲባል የኔቶ ተስፋፊነት ይቁም! ወደ ጦርነት የገቡትም ሩሲያና ዩክሬይን ወደ ዕርቅ ይምጡ!›› የሚል ድምፅ ማሰማት አይበዛበትም፡፡

ስለጎጂና ተጎጂ እያሠላሁ ይህ ቢሆን፣ ያ ባይሆን እያልኩ የቀባጠርኩት የአጥፍቶ መጥፋት ባልተሰበረበት አድማስ ውስጥ ሆኜ ነው፡፡ እምቦቲቶ ሻጭ ኩባንያ እስከ ማስወጣትና የጁዶ ቀበቶ ‹‹እስከ መንጠቅ›› ድረስ ምንም አይቅረኝ ያለው ‹‹ለሰው ልጅ አሳቢው›› ምዕራባዊው ዓለም ሩሲያን ወደ አጥፍቶ መጥፋት ኬላ እየገፋት ነው፡፡ ዓለምን ሊያቃጥል የሚችል መሣሪያ በታጠቀ ኃይል ላይ ይህ ሁሉ አድማ ሲደረግ በዝምታ እያየ ያለው ዓለምም ህልውናውን ወደ ገደል አፋፍ እየወሰደ ነው፡፡ በጊዜ የሚባንን ታጥቶ ኬላው ከተሰበረ ስለጎጂና ተጎጂ ማውራት የሚቻልበት ዕድል ስለመኖሩ ማንም እርግጠኛ ሆኖ መናገር አይችልም፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

የአዛርባጃንን ብሄራዊ ቀን በአዲስ አበባ በድምቀት ተከበረ

የአዛርባጃን ኤምባሲ  የአዛርባጃንን ብሄራዊ ቀን በትላንትናው ዕለት አከበረ። ሰኞ...

የመንግሥትና የሃይማኖት ልዩነት መርህ በኢትዮጵያ

እንደ ኢትዮጵያ ባሉ አገሮች የሃይማኖት ተቋማት አዎንታዊ ሚና የጎላ...

ሐበሻ ቢራ ባለፈው በጀት ዓመት 310 ሚሊዮን ብር የተጣራ ትርፍ ማግኘቱን አስታወቀ

የአንድ አክሲዮን ሽያጭ ዋጋ 2,900 ብር እንዲሆን ተወስኗል የሐበሻ ቢራ...