በዮሴፍ ዓለሙ
እንደ ዓባይ ሸለቆ ተቅዘምዝመን ተሠልፈን ታክሲ እየጠበቅን ነው። ጉዞአችን መገናኛ ተጀምሮ ሲኤምሲ ይጠናቀቃል። ታክሲዋ ጭና ከሄደች ከግማሽ ሰዓት በላይ ሆኗታል። መሰሎቿ ግን ተመካክረው ድራሻቸውን ያጠፉ እስኪመስል ድረስ ጭር ብለዋል። አንድ ሽማግሌ፣ ‹‹ልጆቼ ምን ይሆን ገና ከረፋዱ ጭር ያሰኛቸው?›› ሠልፈኛውን ጠየቁ። ከሠልፈኛው መካከል አንድም ደፍሮ እጁን ያወጣ አልነበረም።
ሁሉም ያልሰማ መስሎ ዝም ጭጭ አለ። አጠገባችን በቁሟ አፈር የበላት ላዳ የሚወለውል አንድ ጎረምሳ ተሽሎ፣ ‹‹አባባ… በዚህ ሰዓት መደበኛ ታክሲዎች ዓድማ ላይ ናቸው፣ አይመጡም፤›› ብሎ ተስፋችንን በአጭር ሊቀጨው ሞከረ። ሽማግሌው ሽማግሌ ብቻ አይደሉም፣ አርበኛም ሳይሆኑ አይቀርም። ዋዛ ፈዛዛ ንግግር የሚፀየፉ ዓይነት ሰው ናቸው። ሽማግሌው ፈርጠም ብለው፣ ‹‹የምን ዓድማ ነው በል?›› ሲሉ ጎረምሳውን መልሰው ጠየቁት። ጎረምሳውም ‹‹ይሰሙኛል አባባ! ሁለት ዓይነት ታክሲዎች አሉ ስልዎት። መደበኛና በራሪ እም… አሁን አሁን በራሪዎቹ ታክሲዎች መስመር ላይ አይታዩም። ከጠፉ ሰነባብተዋል። ሌሎች ተረኞች ተተክተው ሜዳውም ፈረሱም የእኛ ነው በሚል ያለገደብ ይኸው ይፈነጩበታል። አባባ… ይህ የታክሲዎች የመስመር ድልደላ ሥርዓት ለከፍተኛ መድሎና ችግር የተጋለጠ ለመሆኑ አይጠይቁኝ። ይህ የተበላሸ የምደባ ሥርዓት ደግሞ መደበኛ ታክሲዎችን ሳያስኮርፋቸው አልቀረም፡፡ ልብ በሉልኝማ አባባ መደበኞቹ ታክሲዎች በአንዲት መስመር በፖሊስ ጥፊ ተኮንነው ሲመላለሱ ይውላሉ። ተረኞቹ ታክሲዎች ግን በፈለጉት መስመር ሲጋልቡ ይውላሉ። ይህ መድልኦ የመንገድ መጨናነቅ ተጨምሮበት ለመደበኛ ታክሲዎች ትልቅ ምሬት የፈጠረ መሆኑ እውነት ነው። በዚህ ምክንያት መደበኛ ታክሲዎች በየቀኑ ሰዓት እያዩ ዓድማ ይመታሉ። አባባ… በዚያ ላይ የበርጫ ሰዓቷም እኮ አለች። ስለዚህ በተረኞች የመድልኦ ቅሌትም ይሁን በበርጫ ሕግ መደበኛ ታክሲዎች በዚህ ሰዓት ዓድማ ላይ ናቸው…›› ብሎ እንቅጩን ነገራቸው። የምርም ይህ የላዳ ሾፌር ተስፋ አስቆራጭ ፍጥረት ነው። በአንድ በኩል ግን ጎረምሳው እውነታውን ተናግሯል።
ከሠልፈኛው መሀል አንድ ጨብራራ ወጣት፣ ‹‹ምድረ ጀለስ፣ መደበኛ ታክሲዎች አርምሞ ላይ ከሆኑ ታዲያ ማንን ነው የምንጠብቀው? እኮ ተረኛ ታክሲዎችን? ይህ ሊሆን አይችልም፡፡ እንደፈለጉ የሚጋልቡ ተረኛ ታክሲዎችን ከዚህ በኋላ ማመን ጅላጅልነት ነው። ሲንቀዥቀዡ የማናውቀው ጎሬ ወስደው ቢደፉን ምን ዋስትና አለን? ሆሆሆ…›› ከሠልፉ አባልነቱን ሰርዞ በእግሩ ጉዞ ጀመረ፡፡ ይህ ጨብራራ ወጣት የዋዛ አይደለም። ጥሩ ልብ አለው። እውነት ነው ተረኛ ታክሲዎች የቁራ መልዕክተኛ እንጂ እርግቦች አይደሉም። በራቸውን ከፍተው መደመር እያሉ ሲጣሩ የምር አገልጋይ ይመስላሉ። ደግሞ የወያላው ቂቤ ምላስ አይጣል። እውነት ደምረው ያሰብንበት ቢያሻግሩን ኖሮ በየጎዳናው የፀሐይ ቀለብ ባልሆንን ነበር። ኧረ እንዲያውም እንደ መስቀል ወፍ ብቅ እልም እያሉ ሳንቲም ከማሳደድ ውጭ የረባ ሲያገለግሉን አላየንም።
እንዲህ ዓይነት ተረኝነትና ራስ ወዳድነት ያሳሰባቸው እኚህ አርበኛ ሽማግሌ፣ ‹‹ልጆች ያም ሄደ ይህም መጣ፣ የቀን ህልማችንን ለመፈጸም መንገድ ላይ ቢረፍድብንም በእግራችንም ቢሆን ተጉዘን አመሻሽ ላይ ያሰብንበት መድረስ መቻል አለብን። ዓድዋ ይናገር። በባዶ እግራችን ተጉዘን ህያው ፍሬ አፍርተንበታል። ነጭ ጫማ አድርጎ በጫማ ሊረግጠን ቢመጣ በባዶ እግራችን ተጉዘን ተዋግተን የጥቁርን ሰውነት ዓድዋ አምባ ላይ በደም ቀለም ላይደበዝዝ አንዴ ጽፈነዋል። የነጭ ‹ትምክተኛ ሰውነት› ዓድዋ ላይ ላይመለስ ተንኮታኩቷል…›› አሉ። ድንቅ ንግግር ነበር። ሠልፈኛውን ያነቃቃ ንግግር። እውነት ነው ሐበሾች ነን። ሥልጣኔን ጀምረን የቋጨን ሕዝቦች። አክሱምና ላሊበላ የፕላኔታችን ሥልጣኔ መሠረትም መቋጫዎችም ናቸው። አዎ አበሾች ነን፣ ቀኖቻችን በተስፋ የተሞሉ። ተስፋ እየተመገብን የምንጠግብ። በተስፋ ኖረን የምናልፍ። የተስፋችን ዳራ ከደመና በላይ የተሰወረ የተስፋ ማሳዎች ነን። በእርግጥ በተስፋችን መሀል ደንቃራዎች የሉም ማለት አይደለም። ሆኖም ግን አመሻሽ ላይ ከጀንበሯ ጋር ፈገግ የምንለው እኛው ነን አልያም ከንጋቷ ጮራ ጋር የመጨረሻዋን ሳቅ የምንስቀው እኛው ነን።
አርበኛው የጃንሆይ ባርኔጣ ያደረጉ ቆፍጠን ያሉ ናቸው፡፡ ‹‹ወይኔ! የኮስትር አሽከር እም! የዓባይ በረሃ ይናገር ማን እንደ ነበርን! አጎይ መሰንበት! ኧዲያ! በእግሬ ባዘግም እስካሁን እደርስ ነበር። አጓጉል ተስፋ ቤት አያሰፋ …›› አሉ ቁጭትና እልህ እየተናነቃቸው። የአርበኛው ቁጭት የተጋባባት አንዲት ኮረዳ ውስጧ የተቃጠለውን አየር በረዥሙ እያስወጣች ጭውውቱን ተቀላቀለች፡፡ ‹‹አይዞን አባባ! ትንሽ ታግሰን እንያቸው እስኪ። ተረኞቹ ታክሲዎች እኮ አመላቸው አይዘለቅም። እንዴት እንደምንግባባ ፈጣሪ ይወቅ። ቀሩ ብለን ጉዞ ስንጀምር ለአፍታ ብቅ ብለው ተስፋ ይለኩሱብንና ከጉዞአችን ያደናቅፉናል። መጡ ብለን ደግሞ በተስፋ ቆመን ስንጠብቃቸው ወዲያሁኑ የውኃ ሽታ ይሆናሉ። በዚያ ላይ ቁማራቸው አያድርስ። አባባ… ሰምና ወርቅ መጫወት እወዳለሁ…›› ሽማግሌው ፈለጉም አልፈለጉም ቆንጅት ቅኔዋን እንዲህ ስትል ተቀኘች
ጥምቀት ተጨፍሮ፣ ደ‘ሞ ሌላ ጥምቀት
ተረኛ ነሽ አሉ፣ እስክስ በይበት
ዛፍ ቅጠሉን ለብሰሽ፣ ተመላለሽበት
በነገራችን ላይ ቆንጅት አፍ እንጂ ጆሮ የላትም፡፡ አንዴ መናገር ከጀመረች እንደ ሐምሌ ዝናብ ማባሪያ የላትም። ግን ደግም የማትሰለች ውብ ነች። ‹‹እም… አባባ፣ የእነዚህ ተረኛ ታክሲዎች መታወቂያ ታርጋ የተለየ ሊሆን እንደሚችል እገምታለሁ። ጥሩምባቸው ሳይቀር የሆነ ቋንቋ ቢጤ አለው። ደ‘ሞ እኮ ፀባያቸው። ተባይ ምን እጅ እግር አለው። ፀባይ ቢነሳቸው፣ ምን አለ መድኃኒት፣ ፀበል ቢያድላቸው…›› ብላ ሞባይሏን ከዘንቢሏ አውጥታ ቀጠለች።
እኔም ከቆንጅት ዕይታ ውጪ የተለየ ምልከታ የለኝም። ተረኛ ታክሲዎች ይሰማል? እባካችሁ ተራ መጠበቅንም ልመዱ። እኔ ብቻ ልፍጀው የትም አያደርስም። ለብቻ ያስቀራል፡፡ ወገን ያሳጣል። የወንዜ ሰው ሆዳምነትን እንዲህ ሲል ይኮንናል፡፡ ‹‹ሆዳም ሰው ፍቅር አያቅም። ሆዳም ታሪክ የለውም። ከሆድ ስም ይሻላል። ብቻውን የበላ ብቻውን ይሞታል… እንዲህ ከመባል ያድነን። ተረኛ ታክሲዎች ‘ንብን‘ እስኪ ለአፍታ ተመልከቷት። ትናንት ወለላ ስትቀዳ እንዳልነበር ዛሬ ምን አለ የምታሸተው የአበባ ቅንጣት እንኳ ባገኘች። ‹‹የዓይናችሁ ቀለም አላምር አለኝ…›› እያለች ከአበባ አበባ ስትዘል የነበረችው ንግሥት ቀፎዋን ረግጣ ወጥታ ትቢያ ላይ ተፈጠረች። አበባውም ቀርቶባት ኧረ ምን አለ ኩሬ ውኃ እንኳ ባልደረቀባት፡፡
ከውስኪም ውስኪ እመርጣለሁ ስትል ውኃ ጥም ሊቆርጥህ ስለሚችል አገር በቀል ጠጅ ልመድ። ማር ወይም ስኳር ከጠፋ ደግሞ ጠላም ቢሆን ልመድ። ውኃ ጤና ነው በንግሥናህ ወቅት ስትንቀባረር የቀባህ ያደግክበት መደብ ላይ ሊወረውርህ ሥልጣን እንዳለሁ አትርሳ፡፡ መደብ ላይ ተወልዶ ያደገ ልጅ የእናቱን መደብ አያፈርስም። አልጋ ሠርቶ ይመቻታል እንጂ።
‹‹ማታ ማታ ሲጮሁ እኮ ሺሕ ይመስላሉ›› እያልክ በእንቁራሪቷ ተረት የእናትህ ቁስል ላይ ጨው የምትጨምር ከሆነ፣ አንተ የጥፋት ልጅ ነህ። ተረኛ ታክሲዎች ከእናቶች መቀነት ስባሪ ዲናር አትንኩ። ይህን አመላችሁን ምሽቱ ሳይቀድማችሁ አሁኑኑ በዕንቁላሌ… በሉት። አለበለዚያ እመኑኝ ዕድሜአችሁ የቀንድ አውጣ ይሆናል። ተረጋግታችሁ መጓዝ ካልቻላችሁ ቁልፉን ለሚችል ስጡት። ‹‹አላዋቂ ሳሚ ዓይን ይጠነቁላል›› ይባል የለ። ስንቱን የደሃ ቤት ጨፈለቃችሁት። የቆመ ሐውልት አይቀራችሁ። እስኪ ጉንዳኖችን ተመልከቱ። ዕልፍ አዕላፍ ሆነው ጎዳና እየሠሩ ሲግተለተሉ ግጭት የሚባል ነገር አያውቃቸውም። ደግሞ ቤታቸውን ቀርቶ ጎዳናቸውን ሊረግጥ የሞከረ የውጭ ኃይል ዋጋ ይከፍላል። ወረንጦ የመሰለ ጥርሳቸው ጠላቶቻቸውን ለመፋለም ድንቅ መሣሪያ ነው። ጉንዳኖች በሰፈራቸው የውስጥ ጉዳይ ለውጭ ኃይሎች ቦታ የላቸውም፡፡ የማንንም ዕርዳታ አይፈልጉም።
እናንተ ተረኛ ታክሲዎች ፈጽሞ ዓይን አላችሁ አልልም፡፡ መሀል ጊዮርጊስ አደባባይ ላይ ትልቁን ሐውልት ሳይቀር ካልዘረርነው የምትሉ ጉደኞች እኮ ናችሁ፡፡ እንዴት እዚህ ድረስ ማየት ተሳናችሁ? ጥቁር ሰው አደለም ፊንፊኔ ጣሊያን ሆኖ ይታያል፡፡ ‹‹ለሕፃን ልጅ ብርጭቆ አይሰጡትም›› ያለው የተረት አባት ይህችን አንድ እውነት ተናግሮ አለፈ፡፡ ስንት ጊዜ ፍሬን በጥሳችሁ ልትደረምሱት ተገለገላችሁ? ወይ እህል ውኃ! በእውነት መዛለቂያችንን ያብጀው! ደግሞ እኮ ‘ቁማር ተጫወትን‘ የምትሉት ጥሬ ወሬአችሁ ነው የጠነዛን። ቆንጅት ድረ ገጽ ላይ ጥልቅ ከማለቷ በፊት፣ ‹‹አባባ… ደግሞ ታዘቡልኝማ፡፡ ሾፌሩ አፍንጫ ሥያሉ ጥቅሶችና ወያላው አመላቸው አንድ ዓይነት ነው፡፡ ካልዘረፍናችሁ አትወርዷትም በሚል ይናበባሉ፡፡ ጥቅሶቹ… መልስ ለጥያቄ ብቻ ነው‘ ብለው አፋችንን ይዘጉታል፡፡ እዚህ ጋ ሁለት ትልልቅ መብቶቻችን አጥተናል። የመናገርና ንብረታችንን የመጠየቅ መብት ሲቀጥል ወያላው ደግሞ … ‹መሽቷል ታሪፍ ጨምሯል› የሚል ሕግ አውጥቶ አዋጅ ይነግራል፡፡ ከዚህ በኋላ አዳሜ ወለም ዘለም የለም፡፡ ኪሱን አራግፎ መውረድ ብቻ ይሆናል አቅሙ ካልሆነ…›› ቆንጅት ንግግሯን ሳትቋጨው ጥላዋን ዘርግታ አየሩን ለማቀዝቀዝ ሞከረች፡፡ የልጅቷን ሐሳብ እኔ ልቋጨው። ካልሆነ ወያላውም፣ ጥቅሶቹም ክርናቸውን አሳብጠው ያፈጡብናል፡፡ ምዕመኑም ንብረቱን ተነጥቆ፣ የመናገር መብቱን ጭምር አጥቶ ብቻውን እየቀባጠረ ጉዞውን ይቀጥላል። ይህ አመል ሰውነት አይደለም፡፡ ከአሮጊት መቀነት ነጥቆ የሚበላ ወያላ ወይም ሾፌር ከዱር ጅብ በምን ይለያል? እኛ እኮ ኢትዮጵያዊ ነን ተግደርድረን የምንቀምስ፣ በመሶብ ተካፍለን ሺሕ ዓመታትን የኖርን ሕዝቦች፡፡ ታዲያ አሁን አሁን የምናያቸው ታክሲዎች ይህን አመል ከየት አመጡት? ኢትዮጵያዊ ናቸው ለማለት እኮ በጣም ያሳፍራል፣ ያስፈራልም፡፡ ሿሿዎቹንማ ፈጣሪ አያጋጭ፣ ፖሊሱም ተረኛ፣ ታክሲዎቹም ተረኛ፣ ነጋዴው ተረኛ ዘይት የሚጨልጥ፡፡ ይህ መግለጫ ግን መልካሞችን አይጨምርም፡፡ ይልቁንም ምሥጋና ይገባችኋል።
ደግሞ የሚገርመው እነዚህን ተረኛ ታክሲዎች ታርጋ ቆልፎ የሚለቃቸው ሥምሪት መሪ በቴሌቪዥን መስኮት ላይ ዛሬም ኢትዮጵያ እያለ በእናቶች አንጀት ላይ የቃላት ቼዝ ሲቆምር የሚውል ነው፡፡ ሥምሪት ወይ ተረኛ ታክሲዎች፣ ድንቄም ቁማር ፊንፊኔ እስክትወለድ አዲስ አበቤ ጎመን በጨው እየበላ እንዲያምጥ ሲቀልዱበት፣ አዲስ አበቤ ግን አሁንም እጁን አጣጥፎ ይቁለጨለጫል፡፡ እንጨት በእሳት ላይ ሲቆመር ከማየት በላይ ምን አስቂኝ ነገር ሊኖር ይችላል? አፉ በሉኝ፡፡ የልጅ ነገር ትንሽ ቀላቀልኩ መሰለኝ፡፡ አሁንም ቅድምም ጎመን በጨው እየቀረበልኝ አትቀላቅል እንዴት ይባላል? አሻንጉሊቱን የተቀማ ሕፃን አሻንጉሊቱን እስኪያገኝ ድረስ ማልቀሱን አያቆምም። ለማንኛውም አስተውል ወዳጄ፣ አዲስ አበቤ እንጂ አዳነች አበቤ ብለህ አንብበህ ጉድ እንዳታደርገኝ፡፡
ቆንጅት ከድረ ገጽ መልስ፣ ‹‹እም… እኔ የምለው አባባ ዘይታችንን የጨለጠው ሌባ ምነው እስካሁን አልጮህ አለ? ለነገሩ አውቆ የተኛን ቢቀሰቅሱት ምን ጆሮ ሊኖረው? ጉድ እኮ ነው መሃል አራዳ ተወልደን አድገን የዳር አገር ሕፃናት ሠፈራችን ድረስ መጥተው አራዳ አራዳ ሲጫወቱ ከማየት በላይ ድፍረት ከየት ይመጣል? ወይ ጊዜ ደጉ መጀመሪያ ቢቆላ ቢቆላ የማይበስል ጥሬነታቸውን መላ በዘየዱለት፡፡ ለማንኛውም ምን እንደ ደገሱልን ባይጠፋንም ታግሶ ማየቱ ከቁጭት ያድናል። ደግሞስ የታገሰ ፍሬ አያጣም ይባል የለ…›› ቆንጅት ዳታ ዘግታ ፋይሎቿ ላይ አተኮረች፡፡ ማንጋጠጤ ትክክል ባይሆንም ፋይሎቿ ላይ ዓይኖቼን ወረወርኩ፣ ስለላዬ ተሳክቶ የቋጠረችውን ቅኔ ዘረፍኳት፣
እንግዳ ተቀባይ፣ የአብርሃም ልጅ አገር
ቤት ለእንቦሳ ብትይ፣ ተቀብዬሽ ነበር
የእንግዳ ቤተኛ፣ ሆንሽብኝ ባላገር
ይህች ቆንጆ ሰምና ወርቅ ፍጥረት ነች፡፡ የእናንተን ዕይታ ባላውቅም ልጅቷ ባለቅኔ ነች፣ የቅኔውን ትንታኔ ለእናንተ ልተወው፡፡ እኔ ግን ‹‹ትዕግሥት›› የሚለው የልጅቷ ሐሳብ ላይ ትንሽ መቆየት ወደድኩ። ልጅቷ እንዳለችው ትዕግሥት ፍሬ አለው፡፡ የታገሰ ፍሬ ማጨዱ አይቀርም፡፡ ነገር ግን ልክ ሊኖረው ይገባል። ትዕግሥት ሲባል እጅን አጣምሮ ብቻ መጠበቅ እንዳልሆነ ትናንት በደንብ ተምረናል፡፡ እጆቻችን እየሠሩ፣ እግሮቻችን እየሮጡ ነው መታገስ ያለብን፡፡ መፃያችን ሊጠራም ሆነ ሊደፈርስ የሚችለው ዛሬ በሮጥነው መጠን ነው። በደንብ ሮጦ ልምምድ ያደረገ አትሌት ጥርት ያለ ወርቅ እየጠበቀው ለመሆኑ ብዙ የሚያጠራጥር ነገር አይደለም። ያልሠራ ደግሞ ነሐስም ሊጎሽበት ይችላል። ነሐስ አይደለም ሮጦ መጨረስም ሊቸገር ይችላል። ደግም በግል ከመሮጥ በቡድን መሮጥ የተሻለ ውጤት እንዳለው ከአትሌቶቻችን ታሪክ ብዙ ልምድ ያለን ሕዝብ ነን፡፡ እስኪ የሻለቃ ኃይሌ ገብረ ሥላሴንና የአንበሳው ቀነኒሳ በቀለን የጀግንነት ውሎ በወፍ በረር ህሊና ቃኝተን እንመለስ፣ እኔ የታየኝን ልናገር፡፡ ሁልጊዜ ጠዋት ተነስተን በቡድን መሮጥ፣ ይህን የቡድን ሥራ ተለማምደን ሕይወት ካደረግነው ጨለማው የፈለገ ቢሆን ሊበረታብን ሥልጣን የለውም። ይልቁንም ጥሶ ማለፍ ቀላል ይሆናል። እመኑኝ፣ ይህን ፊታችን የተጣደ ተረኛ ደመና ሮጠን ለመቅደም በቡድን መክነፍ መቻል አለብን። እንደዚያ ሲሆን ይህን ጨለማ መውጋት የሚችል ዓይንም ጉልበትም ይኖረናል። ‹‹ተመሳሳይ ላባ ያላቸው ወፎች አንድ ላይ ይበራሉ›› ይባል የለ? በዚህ ወቅት በጣም የምገዛው ሐሳብ ነው፡፡ መፃያችንን እንዳመጣጡ ለመቀበል አንድ ላይ መብረር ግድ ይለናል። ተመሳሳይ ወፎች አንድ ላይ ሲበሩ ለቁራዎች ሙቀት አይሰጣቸውም፡፡ ምልከታዬን በቅኔ ልሰረው፣ ቆንጅት እየጠበቀችን ነው፡፡
ወሬሽ ጠመዝማዛ፣ የወንዝ ጅረት
ዋርካ ፅዱን ደፍተሽ፣ ተሳፈርሽበት
ለማንኛውም ቆንጅትን ስሙልኝማ፣ ‹‹እም… አባባ፣ የምር አርበኛ ነዎት ልበል? ላደረጉት የጃንሆይ ባርኔጣ ትልቅ ክብር አለኝ፡፡ ይህንን ባርኔጣ ከዚህ ትውልድ ይልቅ ጣሊያኖች በደንብ ያውቁታል፡፡ እባክዎትን አንድ ‹‹ሰልፊ›› ፎቶግራፍ ላስቀር ፍቃድዎት ከሆነ። እም፣ አባባ ደግሞ እኮ በስንት ገላጋይም ቢሆን ዓድዋን ካከበርን ወር እንኳ አልሞላንም፡፡ ማለቴ ጊዜውን የሚመጥን ታሪካዊ ቆብ አድርገዋል ማለቴ ነው…›› ሽማግሌውም ፎቶ ለመነሳት ተስማሙ ቆንጅት ከአርበኛው ጋር ‹‹ሰልፊ›› እየተነሳች፣ ‹‹እኔ የምልዎት አባባ፣ ዓድዋን የሚፀየፍ ማኅበረሰብ ኢትዮጵያን የመምራት ሞራል እንዴት ሊኖረው ይችላል?›› ብላ ጠይቃ ስታበቃ ተመልሳ ትኩረቷን የአርበኛው ባርኔጣ ላይ አድርጋ ቀጠለች፡፡ ‹‹ጃንሆይ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ከፕሬዚዳንት ሩዝቬልት ጋር በሺሕ ፈረንጅ ታጅበው በአሜሪካ ጎዳናዎች ሲፈሱ ግርማዊነታቸው በዚህ ቆብ ደምቀው እንደነበር አስታወሳችሁ አባባ፡፡ ኢትዮጵያዊነት በታላቋ አሜሪካ ከፍ ብሎ የተውለበለበበትም ጊዜ እንደነበር መካድ አይቻልም፡፡ ከዚህ ቆብ ጥላ ሥር ምን ያህል ነጭ ይሰግድ እንደነበር ድርሳናት ላይ ሳይቀር ሥዕሎችን ተመልክቻለው፡፡ ድረ ገጽ ላይም ብዙ ፎቶግራፎች የማየት ዕድል ገጥሞኛል…›› ቆንጅት የተዘናፈለ ፀጉሯን በጣቶቿ እያበጠረች ከሽማግሌው ጋር ‹‹ሰልፊ›› ተነሳች፡፡
በነገራችን ላይ ይህች ውብ ኮረዳ ግዮናዊት ነኝ ትለናለች፡፡ ለዚህ ደግሞ የአንገቷ ማኅተብ ላይ ‹ኢትዮጵ ግዮናዊት› የሚሉ በብር የተጌጡ ፊደሎች ይነበባሉ፡፡ ግዮናዊት መሆኗንና ስሟም ‹‹ኢትዮጵ›› ሊሆን እንደሚችል ወደፊት እንጠብቅ፡፡ ልጅቷ የሕይወትን ሰምና ወርቅ ከግዮንና ከጣና ቁርኝት ያመሰጠረች ልትሆን እንደምትችልም ነገረ ሥራዋ ያሳብቃል።
አንዴ ማውራት ከጀመረች ደግሞ እንደ ዓባይ ሸለቆ መቋጫ የላትም። የተሰማትን ያለ ገደብ በነፃነት መናገር የምትወድ ነች፡፡ አዳመጧትም አላዳመጧትም ሐሳቧን ሳትፈራ ትናገራለች፡፡ ለዛፍ ቅጠሉ ሁሉ የምታወራ እስኪመስል ድረስ ታወራለች፡፡ ከራሷም ጋር በነፃነት ታወራለች፡፡ ሐበሽና ሐሜት አበደች ቢሏት ነው፡፡ ወይ ከመጤፍ! እሷም ግድ የሚሰጣት ዓይነት አይደለችም፡፡ በነገራችን ላይ አንዳንድ ጊዜ ሕዝብ አያብድም አይባልም፡፡ ሕዝብ አበደ ያለው ዕብድ ደግሞ ጤነኛ አይሆንም አንልም አመክኒዮውን ልናገር። ሕዝብ አበደ ያለው ሰው ‹‹ሱፐር ኢጎ›› ላይ ሊሆን ስለሚችል የተገላቢጦሽ ዕብድ የሚል ታርጋ ሊሰጠው ይችላል፡፡ ማለትም አበደ የተባለው ግለሰብ ከሕዝቡ አስተሳሰብ ስለሚልቅ የሚረዳው ሲያጣ ከራሱ ጋር ብቻ ማውራትን ሕይወት አድርጎት ሊቀጥል ይችላል።
ለማንኛውም ወደ ልጅቷ ልመልሳችሁ አፈር ስሆን ስሙልኝማ፡፡ ከከንፈሯ አንዳች ወይን ይመነጫል፣ ‹‹አባባ ስሜን እኮ አልጠየቁኝም ኢትዮጵ እባላለሁ። ለነፃነት ትልቅ ዋጋ እሰጣለሁ፣ ነፃነት ተፈጥሮዓዊ ነው፣ ማንም ሊሰጠን አልያም ሊነሳን አይችልም፡፡ በሥነ ፍጥረት ርዕዮት ዓለም ነፃነትን የሚያህል ፀጋ ተሰጥቶናል ብዬ አላምንም፡፡ ሰው ህሊናውን የሚያዳምጥ ትልቁ ነፃ ፍጥረት ነው የሚባለውም ይህን ሰብዓዊ ማንነት ተመሥርቶ መሆን አለበት፡፡ ስለዚህ አባባ በኢትዮጵያዊነት ሥነ ልቦና ሙሉ ሆኜ ተሠርቼ እንዲህ ውብ ሆኜ የበቀልኩት፣ አባቶቼ ለነፃነት በሰዋችሁት ደም የነፃነት ጥሜ ተቆርጦ መሆን አለበት፡፡ እኔ ልጅት ‹‹ኢትዮጵ›› የአባቶቸን ህያውነት መቼም እዘክራለሁ፡፡ የነጭ እንክርዳድ በልቶ ጠጥቶ የናወዘ የወሬ ቋት ቢለፈልፍ፣ የጥቁሮች ሁሉ የነፃነት ጮራ የዓድዋው ጥቁር ሰው መሆኔን ሊያደበዝዘው አይችልም፡፡ አይደለም ምኒልክ አደባባይ ዓድዋ አምባ ድረስ ሄጄ የጥቁሮች ሁሉ የነፃነት ቀንዲል ጥቁር ሰው መሆኔን ገና እዘክራለሁ። ከነጭ ዱካ በላይ ዱካዬ ረዝሞ በአደባባይ ቀና ብዬ በነፃነት የቆምኩት፣ አባቶቼ በከፈላችሁት መስዋዕትነት ነው ዝቅ ብዬ አመሠገንኳችሁ፡፡ በዓድዋ ከፍታ ልክ እንዳስብ አድርጋችሁኛልና፡፡ ስለዚህ አባባ ለዚህ ቀን የሚመጥን ስጦታ አለኝ። ድፍረት አይሁንብኝና ‹አባባ ጃኖ› ብዬ ስም ሳወጣልዎት በኩራት ነው። አባባ ቅር ይልዎት ይሆን?›› ልጅቷ ቆንጆ ብቻ አደለችም፣ ታላቅነትንም የተረዳች የልጅ አዋቂም ነች፡፡
ሽማግሌው ጉሮሮዋቸውን እየጠራረጉ፣ ‹‹ኧረ በፍጡም ልጄ፣ በፍጡም እንዴት ሆኖ ቅር ይለኛል ብለሽ ነው። ኧም… በዚህ ስም አጥፊ ዘመን ስም የሚያጠፋ እንጂ ስም የሚሰጥ ተገኝቶ ደግሞስ ቅር ልሰኝ? አባቱን የማይወቅስ ልጅ የተባረከ ነው፡፡ ልጄ ያብዛሽ፣ ስጦታሽን እጅ ነስቼ በክብር ተቀብዬዋለሁ፡፡ ዓድዋን የሚዋጅ ድንቅ ስም ሸልመሽኛል፡፡ ልጄ መቼስ ታውቂያለሽ አይደል እኛም በጊዜያችን የአባት ሐውልት ለማፍረስ የሚያንደረድር የከፋ አሳፋሪ ታሪክ አላወረስናችሁም፡፡ ከአደባባይ የሚለይ የሚያፋልስ የውርደት መንገድ የተውንላችሁም አይመስለኝም፡፡ ነፃና አንድ ትልቅ ሕዝብ እንድትሆኑ የሚከፈለውን መስዋዕትነት ሁሉ ጊዜውን በዋጀ አግባብ ከፍለናል፡፡ አቅማችን በፈቀደው መጠን አንድ ላይ ሰፍታችሁ ደምቃችሁ እንድትኖሩ የሰሰትነው ጉልበትም አልነበረም፡፡ ይህ የምታይው ጎዳና ሁሉ የእኛ አሻራ አለበት፡፡ ታዲያ ነፃነት የማይወድላቸው አንዳንድ ጠባብ ህልሞች እንደ እንጉዳይ በየጊዜው እየፈነዱ ዛሬም ድረስ ባርነትን ይናፍቃሉ። እም… በእነዚህ አደባባዮች እኮ የነፃነት ቀለም ቀይ ቢጫ አረንጓዴ ሰንደቅ ይዘን ለጥቁሮች ሁሉ ወጋገን ሆነናል። ታዲያ ይህን የነፃነት ሰንደቅ ይዘን ነጭ ያልደፈረን ነፃ ሕዝቦች መሆናችንን ዛሬም አንድ ላይ አለማክበራችንን ሳስብ በጣም በጣም አዝናለሁ…›› አባባ ጃኖ በቁጭት አራት ነጥብ የሌለው ንግግር ማሰማታቸውን ቀጥለውበታል፡፡
‹‹ስንት ያልተሄዱ ሰፋፊ ጎዳናዎች ስንት ገና ያልተኖሩ ራዕዮችን ልንሄድ አቅደን ነበር። ነገር ግን እነዚህ ወፍ ዘራሽ ጠባብ ህልሞች ቆንጨራ ይዘው ዛሬም ድረስ ጎዳና እየዘጉ ያደናቅፉናል። እኛ ስንገነባ እነሱ ያፈርሳሉ፣ ሊደረምሷቸው የደገሱላቸው ታሪካዊ ልማቶችስ ቢሆኑ የጋራ መኩሪያ እንጂ፣ የአንድ ማኅበረሰብ እሴትስ ብቻ መቼ አላደሉ፡፡ ታሪክን ደፍረው ቢመረምሩ ኖሮ እነዚህ ታሪካዊ ቅርሶች እኮ የእነሱም አባቶች ጭምር መታሰቢያ ናቸው፡፡ ነገር ግን ይኼ ጎዳና ለይቶ የመዝጋትም ሆነ የመፍሰስ ተረኝነት ምን ያህል እንደጎዳን ተመለከትሽ ልጄ፡፡ ይኼው ቀናችንን ሙሉ መንገድ ዳር ተገትረን ጥላ የሌላቸው ተረኛ ታክሲዎች ስንጠብቅ ጊዜአችን አለቀ። ምድብተኛ ታክሲዎቹ በመስመራቸው ቢፈሱ ኖሮ እኛም በየጎዳናው ተትረፍርፈን ባልተገተርን ነበር። አየሽ ጉብሌ፣ ተራ መጠበቅን እንጂ ተረኝነትን መፀየፍ አለብን…›› አሉ፡፡
‹‹የእኔ ልጅ ጉብሌ፣ መቼም እንግዲህ እኛ አባቶቻችሁ ወፈረም ቀጠነም ብዙ ጎዳናዎችን ቀደን እዚህ ድረስ አድርሰናችኋል፡፡ እነዚህ ተረኛ ታክሲዎች ግን በኢትዮጵያዊነት ጎዳና መላመድ አቅቷቸው ይደናበራሉ፡፡ ልጄ የማትጠገቢ ነሽ፣ ለዛ ያለው ጨዋታሽ ተመችቶኝ እንጂ ወገቤ ይህን ያህል የመታገስ አቅም አልነበረውም። ኡፍ ኡፍ ኡፍ…›› ሽማግሌው ሳል አቋረጣቸው። ቆንጅት ቀጠለች፣ ‹‹አባባ ጃኖ፣ አይዞን! ካልሆነ እኮ የሃይገር ወይም የባቡር አማራጭ አይጠፋም…›› ብላ ለዛ ባለው አንደበቷ ብርታት ሆነቻቸው።
ልጅቷ በውበት ጎዳናም ቢሆን ታይታ የማትጠገብ ነች፡፡ ኧረ እንዲያውም ቆይ እንቅጩን ልንግራችሁና እረፉት፡፡ ከፈለጋችሁ ያችን ሞናሊዛ የምትሏት ቅንድብየለሽ ወንዳ ወንድ ፈረንጅ ሳይቀር ጥሯት፡፡ ከሐበሻ ልጅት እኩል እኮ ከዚህች ውብ ግዮናዊት? ኧረ በፍጡም በየት በኩል ልትወዳደር? ወይ ጥፍሯን የቀለሟን ሚስጥር አባባ ጃኖም ጆሯቸውን ከፍተው ዓይን ዓይኗን እያዩ ነበር በተመስጦ ይሰሟት የነበረ። ልጅቷ ውብ ለዛ ያላት ናት። እንኳን ጎረምሳ ሽማግሌ ታሞቃለች። ከትርምሱ መሀል ሲወያዩ ቁርጥ ወላጅ አባትና ልጅ ይመስላሉ እንጂ፣ ትርምስ ያገናኛቸው መንገደኛ አይመስሉም፡፡ ታዲያ ይችን ቢውጧት የማትጎረብጥ ለስላሳ ወጣት በዓይኑ ደጋግሞ ሳይሳለም ያለፈ አላፊ አግዳሚ ይኖራል ብሎ ማሰብ ዘበት ነው። የእኔስ ቀልብ ቢሆን? የውበት ማዕበል አጠገቤ ቆማ አልተወሰድኩም ብል ማን ያምነኛል? ከውበቷ በላይ ቅንነቷና ልበ ሙሉነቷ ሳይማርከኝ አልቀረም፡፡ ሆኖም ለአፍታ ዓይኖቼን ነቅዬ መገናኛ ዙሪያ ገባውን እንዲቃኙ ሥራ ሰጠኋቸው፡፡ ህሊናዬን ለመጠበቅ መላ መምታቴም ነበር፡፡ ከላይ ካልተፈቀደ በቀር ያዩትን ዳቦ ሁሉ ለመግመጥ መመኘት ትርፉ ኃጢያት ነው፡፡ ለዚያም ነው ያልተፈቀደልኝ ዳቦ ላይ ረዥም ማፍጠጥ የማልወደው፡፡ የማያገኙት ዳቦ ላይ በማፍጠጥ ጊዜ ከማጥፋት የራስን መፈለግ ጥበብ ነው፡፡ ወንዶች አንድ ነገር አስተውሉ ቆንጆ ሴትና ፅጌረዳ ቀጣፊያቸው ብዙ ነው።
በጣም ፈገግ የሚያሰኘኝ የፕላኔታችን ስግብግብነት በቂ ዳቦ ታቅፎ እየገመጠ የሰው ድርሻ የሚያስጎመዥው ሰው፡፡ ዓይኖቼ አሁንም ድረስ በመገናኛ ዙሪያ አንሰራርተው የቤት ሥራቸውን እየሠሩ ነው፡፡ ከሴቶችና ከሽማግሌዎች በላይ ታክሲ በመጠበቅ ጎረምሶችን የሚያክላቸው እንደሌለ ታዝቤያለሁ፡፡ ስንቱ ወጣት የደጋ ጅብራ መስሎ በየጎዳናው የማይታመን ተረኛ ታክሲ በመጠበቅ አንቀላፍቶ ጊዜውን ይገድላል፡፡ ሦስት አራት ፌርማታ ለማይወስድ መንገድ ሰው እንዴት ከግማሽ ሰዓት በላይ ቆሞ ታክሲ ይጠብቃል? ያደለው ጋሸና አላማጣ ድረስ ይዘምታል። በነገራችን ላይ ይህን ከቁራ አፍ ቅንጣት የሚጠብቅ ትውልድ ላስተዋለ መፃያችንን መልካም አድርገው ብሎ ቸር ከመመኘት ሌላ ምን ማለት ይችላል?
ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እየገለጽን፣ በኢሜይል አድራሻቸው [email protected] ማግኘት ይቻላል፡፡