የምዕራብ አፍሪካ አገሮች በተለያዩ ጊዜያት በሚነሱ የርስ በርስ ግጭቶች ከሚፈተኑ ሥፍራዎች ይጠቀሳሉ፡፡ መፈንቅለ መንግሥት፣ ተቃውሞ፣ የርስ በርስ ግጭት የቀጣናው መለያ ከሆነም ሰንብቷል፡፡ አሁን ላይ ደግሞ አገሮቹ ለከፋ የምግብ ቀውስ እየተጋለጡ መሆኑን ሪሊፍ ዌብ ዘግቧል፡፡
የምዕራብ አፍሪካ አገሮች ባለፉት አሥር ዓመታት ውስጥ ያልታየና የከፋ የተባለ የምግብ ቀውስ ውስጥ እየገቡ መሆናቸውንም የተለያዩ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች አስታውቀዋል፡፡
ኦል አፍሪካ ኒውስ እንደዘገበው፣ 11 ዋና ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ ድጋፍ አድራጊ ድርጅቶች በምዕራብ አፍሪካ የተከሰተውን የምግብ ቀውስ አስመልክተው መግለጫ አውጥተዋል፡፡ በዚህም በአገሮቹ ከባድ የተባለ የምግብ ቀውስ መከሰቱንና አፋጣኝ ምላሽ ካልተሰጠ ችግሩ ወደ ረሃብ ቀውስ ሊሸጋገር ይችላል ሲሉ ረጂ መንግሥታት ርብርብ እንዲያደርጉ ጠይቀዋል፡፡
27 ሚሊዮን ያህል የምዕራብ አፍሪካ አገሮች ሕዝቦች ረሃብ ውስጥ እየገቡና 11 ሚሊዮን ሕዝቦች ደግሞ ለአደጋው እየተጋለጡ እንደሆነም ተናግረዋል፡፡
ከአሥር ዓመት በፊት ከነበረው ለረሃብ አደጋ የተጋለጡ ሕዝቦች ቁጥር በአራት እጥፍ የጨመረ መሆኑንም የኦክስፋም ሪጅናል ዳይሬክተር አሰላማ ዳዋላክ ተናግረዋል፡፡
የምዕራብ አፍሪካ አገሮች የፖለቲካ አለመረጋጋት፣ የርስ በርስ ጦርነትና መፈናቀል የሚበዛባቸው መሆኑ ለችግሩ መከሰት አስተዋጽኦ ቢኖረውም፣ ያባባሰው ግን በሩሲያና ዩክሬን መካከል የተፈጠረው ጦርነት እንደሆነም ጠቁመዋል፡፡
ኦክስፋም እንደሚለውም፣ ድርቅና ዝቅተኛ የዝናብ ሥርጭት በማዕከላዊው የሳህል ቀጣና የምግብ አቅርቦትን ቀንሶታል፡፡ በምዕራብ አፍሪካ አገሮች ውስጥም የምግብ ዋጋ በ30 በመቶ እንዲያሻቅብ ምክንያት ሆኗል፡፡
በቡርኪና ፋሶ፣ ኒጀር፣ ቻድ፣ ማሊና ናይጄሪያ እ.ኤ.አ. ከ2015 እስከ 2022 ባሉት ጊዜያት የአስቸኳይ ምግብ ዕርዳታ ፈላጊዎች ቁጥር ከሰባት ሚሊዮን ወደ 27 ሚሊዮን አሻቅቧል፡፡
በሳህል ቀጣና አንዳንድ አካባቢዎች ደግሞ የሰብል ምርት አምና ከነበረበት በአንድ ሦስተኛ ቀንሷል፡፡ ቤተሰቦች ምግብ የማቅረብ አቅማቸው ተሟጧል፡፡ ድርቅ፣ ጎርፍ፣ ግጭትና ኮቪድ-19 በኢኮኖሚው ላይ ያሳረፈው አሉታዊ ተፅዕኖ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች ቀያቸውን ጥለው እንዲፈናቀሉ አድርጓል፡፡
በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ደግሞ ወደሌሎች ቤተሰቦቻቸው ጥገኝነት መግባታቸው የተቀባዮቹንም ኑሮ አስቸጋሪ አድርጎታል፡፡
በቂ ምግብ ባለመኖሩም የተመጣጠነ ምግብ እጥረት እየጨመረ ነው፡፡ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዘንድሮ ከስድስት ወር እስከ አምስት ዓመት ያሉ 6.3 ሚሊዮን ሕፃናት ክፉኛ ለተመጣጠነ ምግብ እጥረት ተጋልጠዋል ብሏል፡፡ አምና በተመሳሳይ ወቅት 4.9 ሚሊዮን ሕፃናት ለተመጣጠነ ምግብ እጥረት ተጋልጠው ነበር፡፡
ቀድሞውንም በቀጣናው ባለው ችግር ላይ በአውሮፓ የተከሰተው ቀውስ ችግሩን አባብሶታል፡፡ የዓለም የምግብና እርሻ ድርጅት እንደሚለውም፣ የምግብ ዋጋ በምዕራብ አፍሪካ አገሮች ብቻ ሳይሆን በዓለም አቀፍ ደረጃ በ20 በመቶ ሊጨምር ይችላል፡፡
ይህም በምግብ ቀውስ የተጎዱ አገሮችን ለመርዳት የሚደረገውን ጥረት ይፈታተነዋል፡፡
በሩሲያና ዩክሬን መካከል የተነሳው ጦርነትም በስድስት የምዕራብ አፍሪካ አገሮች የስንዴ አቅርቦትን ይቀንሰዋል፡፡ ስድስቱ የምዕራብ አፍሪካ አገሮች ከ30 በመቶ እስከ 50 በመቶ የስንዴ ምርት የሚያስገቡት ከዩክሬንና ሩሲያ ነው፡፡
የምግብ መወደድ በአውሮፓም እየታየ መሆኑ ለዕርዳታ የሚፈለገውን ለማሟላት ችግር ይፈጥራል፡፡ በርካታ ረጂ አገሮችም ለአፍሪካ አገሮች የሚያደርጉትን ድጋፍ እንደሚቀንሱ እያስታወቁ ነው፡፡ ከነዚህም ዴንማርክ ከቡርኪና ፋሶ ጋር አብራ ለመሥራት ቃል የገባችውን የልማት ትብብር ማራዘሟ ይጠቀሳል፡፡
(ጥንቅር በምሕረት ሞገስ)