የኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) በምርጫ ቦርድ የተጣለበትን ዕገዳ እንዲነሳለት የሚያስችል ድጋፍ እንዲያደርግለት ለአገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ ጥያቄ አቀረበ፡፡
ከ22 የፓርቲው ከፍተኛ አመራሮች መካከል የ17 የኢዴፓ ብሔራዊ ምክር ቤትና ኦዲት ኢንስፔክሽን አባላት ፊርማ ያረፈበት የድጋፍ መጠየቂያ ደብዳቤ ግንቦት 2 ቀን 2014 ዓ.ም. ማስገባቱን የፓርቲው የቀድሞ ፕሬዚዳንት አቶ አዳነ ታደሰ ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡
ለ22 ዓመታት በትግል ውስጥ የቆየው ኢዴፓ ለወደፊት የአገሪቱ የፖለቲካ ሒደት ተሳታፊ መሆን ስለሚፈልግ እገዳው እንዲነሳለት ጠይቋል፡፡
ለኮሚሽኑ በደብዳቤ ጥያቄ ያቀረበው ፓርቲው የመጠይቁን ግልባጭ ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽጽፈት ቤት፣ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድና ለፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት አቅርቧል፡፡
የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የሕዝብ ግንኙነት ክፍል ፓርቲው ያቀረበው የደብዳቤው ግልባጭ መግባቱን ለሪፖርተር አረጋግጧል፡፡
ኢዴፓ ያቀረበውን ሐሳብ በቦርድ ታይቶ ምላሽ ያገኛል ተብሏል፡፡ ኢዴፓ በብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ‹‹እውነተኛ ያልሆነ ፊርማ አሰባስቧል›› በማለት በምርጫ ቦርድ በኩል መሰረዙን አቶ አዳነ ገልጸዋል፡፡
ፓርቲው ከመሰረዙ በፊት ያላሟላው መሥፈርት ካለ ጉድለቱን አሟልቶ እንደገና እንዲቀርብ ጊዜና ዕድል ሊሰጠው ይገባ እንደነበር ፓርቲው በደብዳቤው አስታውሷል፡፡
የአገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ ሁሉን አቀፍ የምክክር ሒደት እንዲጀመር የሚፈልግ መሆኑ በተለያየ ጊዜ በመገለጹ ፓርቲው የምክክሩ ሒደት ተሳታፊ መሆን እንደሚፈልግ አስታውቋል፡፡
ፓርቲው ማሟላት የነበረበትን 10 ሺሕ ፊርማ ወደ 15 ሺሕ በማድረስ የፊርማ ማሰባሰብ ቢያደርግም የማስተካከያ ጊዜ ሳይሰጠን ተሰርዘናል ሲሉ አቶ አዳነ ጠቁመዋል፡፡
ምርጫ ቦርድ ሚያዚያ 2012 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ 27 ፓርቲዎችን መሰረዙ ይታወሳል፡፡ ከተሰረዙ የፖለቲካ ድርጅቶች መካከል የሆነው ኢዴፓ በልዩ ሁኔታ ሰነድ ካስገቡ ፓርቲዎች ጋር ሰነዳቸው እንዲታይ የተደረገ ፓርቲ መሆኑን መግለጫው ይጠቅሳል፡፡
ኢዴፓ በብሔራዊ ዕርቅ ሐሳብ ዙሪያ የትግል አጀንዳ ውስጥ የተካተተና በዚህም ሰነዶች ሲያዘጋጅ የነበረ ፓርቲ መሆኑን አቶ አዳነ ጠቁመዋል፡፡
ፓርቲው ወደ ምክክር መድረኩ ለመሳተፍ ኮሚሽኑ የበኩሉን አስተዋጽኦ እንዲያደርግ በጠየቀበት ወቅት ልምድ ያለውን ፓርቲ በመድረኩ ማሳተፍ ጠቃሚ መሆኑን እንደሚምኑና ጥያቄውን የማንሳት መብት እንዳላቸው የኮሚሽኑ ኮሚሽነሩ እንደገለጹላቸው በደብዳቤው ጠቁሟል፡፡
ኮሚሽነሩ አክለውም እንዴት ተሳትፎ ማድረግ እንደሚችሉ ወደፊት እንደሚገልጹላቸው ደብዳቤውን ባስገቡበት ወቅት ምላሽ እንደሰጧቸው አክለዋል፡፡
ፕሮፌሰር መስፍን ፓርቲው ይመለስ ወይም አይመለስ በማለት የሚፈቅድ ሕግ አለመኖሩን ገልጸውላቸው ለብሔራዊ መግባባት ውይይቱ ከኮሚሽኑ የሚጠበቁ ተግባራት ካሉ እንቅስቃሴዎች በማድረግ በሒደት እንደሚያሳውቋቸው ተነግሯቸዋል፡፡
ኮሚሽነሩ ይህን የማድረግ በአዋጁ የተሰጠው መብት አይደለም ግን ውጤታማ እንዲሆን ለማድረግ እንደሚሠሩ ገልጸዋል፡፡
ይህን ጉዳይ በተመለከተ ሪፖርተር መስፍን አርዓያ (ፕሮፌሰር)ን በስልክ የጠየቀ ሲሆን፣ በጉዳዩ ላይ ምንም ዓይነት አስተያየት ለሪፖርተር መስጠት እንደማይፈልጉ ገልጸዋል፡፡