- ለሕግ አስከባሪ ተቋማት የተደረገውን ገለጻ አዳመጡት ክቡር ሚኒስትር?
- የምን ገለጻ? አልሰማሁም።
- ስለአገሪቱ ፖለቲካዊ ክስተቶች ከኋላውም ከቅርቡም ተደርጎ ሰሞኑን ጥልቅ ገለጻ ተደርጎላቸዋል።
- እንዴት አልሰማሁም?
- ልብ ስላላሉ ይሆናል። በተለይም ከምርጫ በኋላ ስለተከሰቱ ጉዳዮች የተደረገው ገለጻ በጣም ገላጭ ነበር።
- ስለምርጫ ምን ተባለ?
- ምርጫ 97ን ተከትሎ ማኅበረሰቡ ድባቴ ውስጥ ገባ፡፡
- እሺ በ2002 ምርጫስ?
- ተብሰከሰከ።
- ማን?
- ማኅበረሰቡ!
- ለምን?
- ኢሕአዴግ ከሁለት የፓርላማ ወንበር በስተቀር ሁሉንም በማሸነፉ፣ ይኼ ነገር ምንድነው? ብሎ ማኅበረሰቡ ተብሰከሰከ፡፡
- በ2007 ምርጫስ?
- ተቆጣ!
- ለምን?
- ኢሕአዴግ የፓርላማውን ወንበር በሙሉ አሸነፈ ሲባል ማኅበረሰቡ ተቆጣ። ለውጡም ያኔ ነው የጀመረው ተብሏል።
- በቀጣዩ ምርጫስ?
- ቀጥሎ ስለነበረው ምርጫ ምንም አልተባለም።
- ለምን?
- ለምን እንደሆነ አልገባኝም።
- ኦ… ገባኝ… ገባኝ!
- ምኑ?
- ቀጥሎ ስለነበረው ምርጫ ምንም ያልተባለበት ምክንያት።
- ለምንድነው?
- በኮቪድ ምክንያት ተራዝሞ ነበር።
- እንደዚያ ከሆነ ካቆምንበት መቀጠል እንችላለን፡፡
- ምን ላይ ነበር ያቆምነው?
- ማኅበረሰቡ ድባቴ ውስጥ ገባ፣ ተብሰከሰከ፣ ቀጥሎ ተቆጣ ብለን ነበር።
- እሺ በቀጣዩ ምርጫስ?
- ማኅበረሰቡ አይምረንም!
- ምን?
- እርሶ እንዳሉት ማኅበረሰቡ አይምረንም!
- ምንድነው የምታወራው? እኔ እንደዚያ ወጣኝ?!
- ኧረ ለጨዋታ ያህል ነው ክቡር ሚኒስትር! ቀልዴን ነው።
- ለጨዋታ እያላችሁ ነው የምታናክሱን!
- የምታናክሱን?
- አዎ። ለነገሩ ጥፉቱ የኔ ነው።
- እንዴት?
- ካድሬዎች ናቸው ማኅበረሰቡን የሚያጋጩት ሲባል እየሰማሁ አለመጠንቀቄ የራሴው ጥፋት ነው።
- ኧረ ክቡር ሚኒስትር ጨዋታውን አከረሩት?
- አከረርኩት እንዴ?
- እሺ ይተዉት… ሌላ ጨዋታ ብንጫወት ይሻላል።
- ምኑን ተጫወትኩት!
- ቅድም ወደዚህ ስመጣ አንድ ነገር አይቼ እንዴት አዘንኩ መሰሎት ?
- ምን አይተህ ነው?
- እዚህ መንገድ ላይ ያለው ኤምባሲ በር ላይ ወጣት የለ ጎልማሳ ተሠልፎ ዓይቼ ምንድነው ብዬ ጠየኩ…
- እሺ?
- ለውትድርና ምዝገባ ነው ሲሉኝ አዘንኩ።
- ኤምባሲ ላይ ለውትድርና ምዝገባ?
- እሱ እኮ ነው የሚገርመው። አገሩን በውትድርና እንዲያገለግል ጥሪ ሲደረግ እንዳልነበር ዛሬ የሰው አገር ወታደር ለመሆን ተሠልፎ ስመለከት አዘንኩ።
- እውነት ነው። በጣም ያሳዝናል።
- ለነገሩ ወጣቱስ ምን ማድረግ ይችላል? አገሩን በውትድርና እንዳያገለግልም እኮ በመንግሥት ኃላፊዎች ንግግር ተደናገረ?
- እንዴት?
- ሰሞኑን የተባለውን አልሰሙም?
- ምን ተባለ?
- ወታደሩ ሲኖር ጄኔራል ነው፣ ሲወጣ ደሃ ነው፡፡
- እና ምን አገናኘው?
- ወጣቱ ይህን እየሰማ እንዴት አድርጎ ሠራዊቱን ሊቀላቀል ይችላል?
- ድጋሚ ልታስገባኝ? እኔ አላውቅም።
- ምን አሉኝ?
- እኔ የማውቀው ነገር የለም አልኩህ!
- እንዴት?
- ወንድሜ ከቤት ልትወጣልኝ ትችላለህ?
- እ…
- ውጣልኝ አልኩህ! እንዴት ያለ ካድሬ ነው የገጠመኝ?
[ክቡር ሚኒስትሩ ሰሞኑን የተፈቀደው ፍራንኮ ቫሉታ የውጭ ንግድ አተገባበር ያስገኘው ውጤት በየጊዜው እየተገመገመ እንዲቀርብ ባዘዙት መሠረት የመጀመሪያውን የግምገማ ሪፖርት እያዳመጡ ነው]
- የፍራንኮ ቫሉታ ዕድል በተፈቀደ በሳምንቱ በገበያው እየተስተዋለ ያለው ነገር አሳሳቢ ነው ክቡር ሚኒስትር።
- ለምን አሳሳቢ ይሆናል? ጠቃሚነቱ ተጠንቶ አይደል እንዴ የተፈቀደው?
- ቢሆንም ባደረግነው ግምገማ አዝማሚያው አሳሳቢ መሆኑን ነው ያስተዋልነው።
- እስቲ አዝማሚያውን አቆይና ውጤቱን አቅርብ።
- ጥሩ። በመጀመሪያ ቅኝታችን ትኩረት ያደረግነው ትይዩ ገበያው ላይ ነው።
- እንዴ ለገበያውም ትይዩ መሠረቱ?
- አልገባኝም ክቡር ሚኒስትር?
- ትይዩ ካቢኔ የመሠረቱት?
- ኧረ ወዲህ ነው ክቡር ሚኒስትር?
- ወዴት?
- የውጭ ምንዛሪ ጥቁር ገበያ ማለቴ ነው።
- ታዲያ ለምን ትይዩ ማለት አስፈለገህ?
- በፋይናንስ ሙያ የተሰጠው ስያሜ እንደዚያ ስለሆነ ነው።
- ቢሆንም የሚያደናግር ቃል መጠቀም ተገቢ አይደለም። ለማንኛውም ቀጥል።
- ጥሩ። እንደገለጽኩት ፍራንኮ ቫሉታ መፈቀዱን ተከትሎ ትይዩ… ማለቴ ጥቁር ገበያው በከፍተኛ ደረጃ ጨምሯል።
- ከፍራንኮ ቫሉታ በኋላ ስንት ገባ?
- በአንድ ጊዜ ከ68 ብር ወደ 74 ብር አሻቅቧል።
- ቢያሻቅብም ማንም ጥቁር ገበያ ሄዶ ዶላሩን ስለማይመነዝር ችግር የለውም።
- እንዴት ክቡር ሚኒስትር?
- ዶላር ያለው ሸቀጦችን እንዲያስመጣበት የፍራንኮ ቫሉታ ዕድል ስላገኘ ወደ ጥቁር ገበያ የሚሄድ አይኖርም።
- ክቡር ሚኒስትር ተቃራኒው ነው እየሆነ ያለው።
- እንዴት?
- ዶላር ያለው ሸቀጥ ከማስመጣት ይልቅ ዶላሩን በጥቁር ገበያ እንዲሸጥ ነው የተመቻቸለት። እየሆነ ያለው በተቃራኒው ነው።
- አልገባኝም?
- የአገር ውስጥ አስመጪዎች በተፈቀደው የፍራንኮ ቫሉታ ዕድል ሸቀጥ ለማስመጣት ከአገር ውስጥ ዶላር የማሰባሰብ ሥራ በስፋት ጀምረዋል። ለዚህ ነው የጥቁር ገበያው ዋጋ ባንዴ ያሻቀበው።
- እኛ የፈቀድነው እኮ ከአገር ውጭ በሚገኝ የዶላር ምንጭ እንዲያስገቡ ነው።
- ነው። ነገር ግን ሰብስበው ያስወጡታል። ሰሞኑንም የተያዙ አሉ።
- ምን ሲያደርጉ?
- በአንድ ጊዜ ግማሽ ሚሊዮን ዶላር ወደ ጅቡቲ ሊያስወጡ የሞከሩ አዘዋዋሪዎች በቁጥጥር ሥር ውለዋል።
- ዶላር ከጥቁር ገበያ ሰብስበው?
- በትክክል። ችግሩ አሳሳቢ የሚያደርገው ደግሞ ሌላ ነገር አለ።
- ምንድነው እሱ?
- የሚያስመጡትን ሸቀጥ የሚቸረችሩት ደግሞ ዶላሩን ከጥቁር ገበያ በገዙበት ዋጋ ላይ ትርፍ አስልተው ስለሚሆን የታቀደው የዋጋ ማረጋጋት ዕቅድ አይሳካም።
- ፍየል ወዲያ ቅዝምዝም ወዲህ ሆኗል በለኛ?
- እንደዚያ ነው። በአንድ ጊዜ ባንክና በጥቁር ገበያው መካከል ከ17 ብር በላይ ነው ልዩነት የተፈጠረው።
- ነገሩ ግን ጥሩ ዕድል እንዳለው ይታየኛል።
- ምን ዓይነት ዕድል ሊኖር ይችላል ክቡር ሚኒስትር?
- በባንክና በጥቅሩ ገበያው መካከል የተፈጠረውን ሰፊ ልዩነት የማጥበብ።
- እንዴት ተደርጎ?
- የብር ምንዛሪ ተመንን ዲቫሊዩ በማድረግ!
- እንዴ ክቡር ሚኒስትር?
- አዎ። እንደውም በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ ዓይነት ዕድል ነው።
- ሌላው ዕድል ምንድነው?
- ከአይኤምኤፍ ለመታረቅ በር ይከፍታል።