በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች እንስሳትን የሚያጠቃውን የቆላ ዝንብ ለማጥፋት፣ በዓለም አቀፉ አቶማቲክ ኢነርጂ ተገዝተው ለኢትዮጵያ የተበረከቱ ሁለት ሰው አልባ አውሮፕላኖች (ድሮኖች) እንዲንቀሳቀሱ የሚፈቅድ አካልና የሕግ ማዕቀፍ ባለመኖሩ፣ ለበርካታ ዓመታት በመጋዘን መቀመጣቸው ተገለጸ፡፡
የቀድሞ የቆላ ዝንብና የገንዲ በሽታ መቆጣጠርና ማጥፊያ ተቋም በ2011 ዓ.ም. የዘጠኝ ወራት የዕቅድ አፈጻጸምን ሲያቀርብ፣ ለቆላ ዝንብ ማጥፊያ የሚያግዙ ድሮኖች ተገዝተው ወደ አገር ውስጥ ቢገቡም እየተስፋፋ የመጣውን የቆላ ዝንብ ለመከላከል ጥቅም ላይ ሊውሉ አለመቻላቸውን አስታውቆ ነበር፡፡
ሪፖርተር ሐሙስ ሚያዝያ 13 ቀን 2014 ዓ.ም. የድሮኖቹ ሁኔታ ምን ላይ እንደሆነ፣ የኢትዮጵያ እንስሳት ጤና ኢንስቲትዩት ማብራሪያ ጠይቋል፡፡
የተቋሙ ምክትል ዳይሬክተር ጌትነት አቤ (ዶ/ር) እንዳሉት ድሮኖቹ ከተገዙ ዓመታት ያስቆጠሩ ቢሆንም፣ አሁንም የኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ባለሥልጣን የበረራ ፈቃድ ባለመስጠቱ ወደ አገልግሎት ማስገባት አልተቻለም፡፡
ድሮኖቹ ምንም እንኳ በዋነኝነት ለቆላ ዝንብ መከላከያ በሚል በፋብሪካ የተመረቱ ቢሆንም፣ አገሪቱ ካለችበት ወቅታዊ ሁኔታ አኳያ ለሌላ ዓላማ በሕገወጥ መንገድ ሊውሉ ይችላሉ በሚል ሥጋት ወደ ሥራ ማስገባት እንዳልተቻለ ተናግረዋል፡፡
ይሁን እንጂ ድሮቹን ወደ ሥራ አስገብቶ በቀላሉ በጂፒኤስ በመቆጣጠር ወደ ሥራ ማስገባት የሚችልበት አማራጭ መኖሩንም ምክትል ዳይሬክተሩ አስረድተዋል፡፡
የተገዙት ድሮኖች ወደ ሥራ እንዲገቡ በግብርና ሚኒስቴር በኩል በተደጋጋሚ ደብዳቤ የተጻፈ መሆኑን የገለጹት ጌትነት (ዶ/ር)፣ እየጨመረ የመጣውን የቆላ ዝንብና በእንስሳት ላይ እያደረሰ ያለውን ጉዳት ለመቆጣጠር ድሮኖች ሥራ ቢጀምሩ ሚናቸው ከፍተኛ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
አንድ ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ የኢትዮጵያ ሲቪል ኢቪዬሽን ባለሥልጣን የሥራ ኃላፊ ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ ድሮኖቹ ሥራ እንዲጀምሩ በተደጋጋሚ ጥያቄ የቀበረ ቢሆንም ከአገራዊ ወቅታዊ ሁኔታ ጋር በተገናኘ በሚል ፈቃድ ሊያገኙ አልቻሉም፡፡
በአገሪቱ ፀረ ድሮን መሣሪያዎች ባለመተከላቸውና ድሮኖችም እንዳይንቀሳቀሱ ከሁለት ዓመት በፊት ተዘጋጅቶ የቀረበው ድሮንን የተመለከተ ረቂቅ ሕግ አለመፅደቁ አንድ ምክንያት መሆኑን አክለዋል፡፡
የድሮን እንቅስቃሴን በተመለከተ በዋነኝነት የሚመለከታቸው የሲቪል አቪዬሽን ባለሥልጣን፣ የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት፣ የኢንፎርሜሸን መረብ ደኅንነት ኤጀንሲ (ኢንሳ) ቢሆኑም፣ ሦስቱ ተቋማት እርስ በርሳቸው በመገፋፋት ሕጉ እንዳይፀድቅ ማድረጋቸውን፣ በዚህም ተገዝተው ወደ አገር ቤት የገቡት ድሮኖች አገልግሎት እንዳይሰጡ መደረጉን ተናግረዋል፡፡
ድሮኖቹ በኢትዮጵያ በተለይም በደቡብ፣ በጋምቤላ፣ በቤንሻንጉል ጉሙዝ፣ በአማራና በሌሎች ክልሎች ተፋሰስና ደናማ የሆኑ ቦታዎች በሚበዙባቸው አካባቢዎች የሚገኘውን የቆላ ዝንብ ለማጥፋት የሚረዱ ናቸው፡፡
በቃሊቲ አርቲፊሻል የቆላ ዝንብ ማራቢያ ማዕከል ውስጥ የመከኑ ዝንቦችን በመሸከም በተጠቀሱት ቦታዎች በመልቀቅ የመራቢያ ሒደቱን ሊያዛባ የሚችል ሥራ የሚያከናውኑ መሆናቸውን የገለጹት ምክትል ዳይሬክተሩ፣ ወደ ሥራ እንዲገቡ ቢደረግ በአርሶ አደሩ ሕይወት ላይ አሉታዊ ጫና እያሳደረ ያለውን የቆላ ዝንብና ጉዳቱ እየጨመረ የመጣውን የነፍሳት ሥርጭት መግታት እንደሚቻል አስረድተዋል፡፡