Wednesday, September 27, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -

የተመረጡ ፅሑፎች

እስኪ አንዴ ፈገግ!

ሰላም! ሰላም! ፆሙን በሰላም ጨርሳችሁ ለበዓለ ትንሳዔ ለደረሳችሁ ሕዝበ ክርስቲያን እንኳን በሰላም ፈሰካችሁ፡፡ በዓሉም የደስታና የሰላም ይሁንላችሁ፡፡ ወደ ወጋችን መለስ ስንል ዓለም ሰላም አጥታ በእኛ ‹ኬፍ› መባባል የሚቆጣ ይኖራል እኮ። ምን ይታወቃል? ከፀባችን ብዛት ሰላምታችን ሁሉ ሰላምን በማረጋገጥ ላይ መመሥረቱ ራሱ ቁጣ ማብረድ ነበረበት እኮ። ግን ምቀኛ አያሳጣን ነው መቼስ። የቅናት ዛር የሰፈረበት ሁላ እንኳን በሰው ሰላም በሰው ኪስ ይቃጠል የለ። አንዳንዴ እኮ አለመፈጠርን የሚያስመኘኝ ከተፈጠርኩ ያየሁት ትርጉም የለሽ ክፋት ተቆጥሮ የማይልቅ ሲሆንብኝ ነው። ዘንድሮ ቆጥራችሁ አይደለም ገና ሳትጀምሩት የሚያልቀው ገንዘብ ብቻ ሆኗል። በተረፈ ሌላው ጉድ የሚያልቅ አይደለም። እና ሰላም በራቀን ልክ እኛም የምንመፃደቀው እንደ ግዳይ መቁጠር የጀመርነው እኩይ እኩዩን ሆነ። የትንሳዔው ሰሞን ደግሞ ይብስብናል። መቼ ዕለት አንድ ወዳጄ ከአንዱ ወደ አንዱ ድለላ ስከንፍ አግኝቶኝ ‹‹ጫረው!›› አለኝ። ‹ፀብ አጫሪ መንገዱን አጣቦ ዓለምን አስጨንቆ ይዟት ሳለ ሌላ ፀብ ጫር ነው የሚለኝ?› ብዬ ልሸሸው ስል፣ ‹‹የት ነው የምትሸሸው? እስቲ ቢራ ልጋብዝህ…›› አለኝ። እኔን ጨምሮ ብዙ ሰው እንደሆነ እንቢ ለማለት ሰበብ ሆኗል የሚፈልገው። ተገኝቶ ነው!

ከኑሮ መክበድ ጋር እያያያዙ ሁሉንም ነገር የበለጠ ማክበዱ ግን ሊገባኝ አልቻለም። ጎበዝ ሳይታወቀን እኮ እያመረርን ነው። በተለይ በበዓል፣ ጉድ እኮ ነው። ብቻ እሺም እንቢም ሳልል፣ ምንም ሳልመልስ ጥዬው ሄድኩ። ክፉም ደግም ሳይወጣኝ አንገቴን ነቅንቄ ጥዬው ሄድኩ። አንዳንዴ ብዙም የማይገባ ነገር ሲገጥማችሁ ፈቀቅ ማለትን የመሰለ ነገር የለም፡፡ ለማንኛውም ተኝቶ መታከም ያለበት ሰው ቁጥር ከኢኮኖሚ ዕድገት አኃዙ በእጥፍ እየጨመረ እንደሆነ እርግጠኛ ሆኛለሁ። አሁን እስኪ ከጦርነት ውስጥ ወጥተን ሰላማዊ ትውልድ መተካት ሲኖርብን፣ ዓባይን ገድበን ጨርሰን በኤሌክትሪክ መንበሽበሽ ሲገባን፣ ቢሰምርም ባይሰምርም የዴሞክራሲ ጭቃ አቡክተን እየማገርን ሥርዓት ማነፅ ሲኖርብን እየናድን፣ ከእኛ ይልቅ እኔን ማለትን ሙጥኝ ማለታችን ሲታወሰኝ ሊያዞረኝ ፈለገ። ግን በስንቱ ይዙርብን! 

 ወትሮ ‹‹እውነት የሚናገር ሰው ጓደኛ የለውም›› አላሉም አፍሪካውያን ጠቃሾች? እውነቴን ነው የምላችሁ ይህችን ጥቅስ እስከ ሸመደድኩባት ቀን ድረስ የመንጋነት እንጂ የመሪነት መንፈስ እንዳለን አላውቅም ነበር። ከነበር አፈንግጦ ‹የለም በዚያ አይደለም! ኑ በዚህ!› ያለ አፍሪካዊ ‹ሶቅራጥስ› እንዳለ ከድለላ በሚተርፈኝ ሰዓት መርምሬ ለማግኘት አንዳንድ መጻሕፍትን ሳገላብጥ ማንጠግቦሽ ታዝባኝ፣ ‹‹ተው ብዙ አታንብብ፣ ታብዳለህ! እኔ ኋላ ከኅብረተሰቡ የተገለለ ባል አልፈልግም። አርፈህ ቅስቀሳ አዳምጥ። ‹አሸነፍን› ሲሉ ‹አበጃችሁ›  በል። ‹አልተሸነፍንም› ሲሉ ‹እንዳላችሁ› ብለህ እለፍ። ነገር አታምጣብኝ…›› ብላ አስፈራራችኝ።  ያነበበና የተመራመረ ሁሉ የሥልጣን ሽሚያ ውስጥ ይገባል ያላት ማን እንደሆነ አላውቅም። ትንሽ ሰነባብታ ደግሞ፣ ‹‹እዚህ ቤት መጽሐፍ የሚባል ነገር ባይ የእኔና አንተ ነገር አከተመ…›› አለችኝ። ካልለመድኩት ብቸኝነት የለመድኩት፣ ምኑ ጣፍጦኝ እንደ ለመድኩትም እንዳላጣራ የተከለከልኩት አብሮነት ይሻለኛል ብዬ ለአንዱ አዟሪ ሸጥኳቸው። ደግሞ ለመሸጥ። እንኳን የራሴን የስንቱን ንብረትና እውነት ሳሻሽጥ አይደል እንዴ የኖርኩት? ታዲያስ!

እንዲያው እርሜን በተጋመሰ ዘመኔ እውነትን ፍለጋ ቆርጬ ብነሳ ተቃውሞ ከቤቴ መጀመሩ አስገርሞኝ ገመናዬን ለባሻዬ ልጅ ሳዋየው፣ ‹‹ደግ አደረገች!›› አለኝ። ‹‹ምነው አንተ የተማርክ ሰው አይደለህ? እንዴት እንዲህ ይባላል?›› ስለው በከፊል ይኼ የትምህርት ጥራት ጉድለት እንኳን በሚኒስትር ሹም ሽረትና በርዕዮተ ዓለም ለውጥ፣ በእንዶድ ቢያጥቡትም አይፀዳ እያልኩ፣ ‹‹መጻሕፍት ውስጥ ሐሳብ እንጂ እውነት ተገኝታ አታውቅማ። ‹በተማረው ባሰ› ‹ባነበበው ከረረ› ሲባል የምትሰማው እኮ ሐሳብ ሸምድደን በሐሳብ ስለምንለያይ ነው። እውነት ግን አብራህ የተፈጠረች ናት። ህሊናህን ስትጠይቀው እውነትን ይጠራልሃል…›› ብሎ  የሚገባኝን አሳንሶ ያልገባኝን አብዝቶ አብራራልኝ። ‹ሐሳብ የሌለባት እውነት እንዴት ያለች ትሆን?› ስል የሚያበላኝን ደላላነት ትቼ የሚያስርበኝን ፍልስፍና ሙጥኝ ልለው ሆነና ነገሩን ተውኩት። በባሻዬ ልጅ አስተያየት ግን ባይዘመርላቸውም ብዙ ሺሕ ሶቅራጥሶች አገሬ እንዳሉዋት አረጋገጥኩ። ማሰብና መናገር እየተነፈጉ አይመስላችሁም ያልዘመርንላቸው? ልክ ነው! 

በነገራችን ላይ አንድ ጥሩ ይዞታ ላይ የነበረ የደረቅ ጭነት ተሸከርካሪ ካጋዛሁት ደንበኛዬ ጋር እንዲሁ በወሬ በወሬ ለልጆች ተረት ስለማውራት ልምድ አንስተን ስንጫወት፣ ‹‹የአሁን ዘመን ልጆች እኮ ተበድለዋል። ከእራት በኋላ ቴሌቪዥን ማየት ይፈቀድልን ብለው መነትረክ ነው የሚያውቁት። አፍ የሚያስከፍት ተረት እንዳልሰማን ኑሮውም ነው መሰል አፍ የሚያስከፍት ተረት ሆኖብን፡፡ የልጅነት ጣዕማቸውን ወላጆች እያበላሸነው ነው…›› አልኩት። ‹‹አይ አንተ፣ የዘንድሮ ልጅ እንኳን ለተረት መቼ ለወተት ይመቻል? አጥንት ብቻ እኮ ነው…›› አለኝ። ‹ምንድነው የሚለኝ? ቋንቋና ምናብ በመለጠጥ ሳንበደል አድገናል ብለን ተኩራርተን ሳንጨርስ በአማርኛ ላንግባባ ነው?› ብዬ ስደነግጥ ቀጠለ። የአስደንጋጩ ብዛት!

‹‹ይኼውልህ እኔ የአምስት ዓመት ልጅ አለኝ። አንድ ቀን አጠገቤ ተቀምጦ የሆነ ነገር እየጎረሰ አስነጠሰው። ‹እደግ› እንደማለት ‹ይማርህ!› ማለት። መውለዴን ብቻ እንጂ ስለልጅ አስተዳደግ ያልተማሩትን ወላጆቼን ያህል እንዳላሰብኩበት ያወቅኩት ያኔ ነው። ያዘኛ። ‹ማን ነው የሚምረኝ?› ብሎ ጀመረ። አንዴ ስቻለሁና ‹ፈጣሪ!› ብዬ መለስኩለት። ‹ምን አጥፍቼ ነው የሚምረኝ?› አለኝ። ብዙ ላስረዳው ሞከርኩ። ስላልተዋጠለት አንድ ጥያቄ ብቻ ጠየቀኝ። ‹አልምርህም ቢለኝ ዝም ትለዋለህ?› አለኝ። ‹ፈጣሪ መሐሪ ነው። እንቢ አይልም› ስለው ‹እንቢ ካላለ ታዲያ መጀመሪያም ጥፋት የሚባል የለም ማለት ነዋ› ብሎ ተነስቶ ሄደ።  ይኼውልህ የዛሬ ልጅ…›› ብሎ ያጫወተኝ ትዝ ይለኛል። ልብ በሉ እንግዲህ ልጁን ያላስተማረ ወላጅ የሚያፈራው እንዲህ ያለውን ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ከመንበረ ዙፋኑ ወርዶ ያንን ሁሉ መከራ ተቀብሎ ከዘለዓለም የኃጢያት ባርነት ነፃ እንዳወጣን አባትየው አለማወቁ፣ ከጨቅላ ልጁ ጋር እንኳን ለመነጋገር አቅም ነሳው፡፡ እኛ እንዲህ ነን!

እኛም እንዲህ ነበርን ወይስ እንጀራ፣ እንጀራ ስንል ‹ሎጂክ› ተነነብን? ምን ያልተነነብን ነገር አለ ዘንድሮ ብዬ እኮ ነው። የማዳበሪያው ትውልድ ነገር ከተነሳ ራሱን በራሱ ማንበብና መጻፍ ያስተማረ ጩጬ ያለውን ልመርቅላችሁ። አንድም በልማትና በፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገቱ ተባባሪ በመሆን፣ አንድም በፈጣን አላቂ ዕቃዎቻቸው የወረሩንን ሰዎች ዕቃዎች እያነሳ ጽሑፋቸውን ያነባል። ሲያነብ ‹ሜድ ኢን ቻይና› ነው። ቢል ያው ‹ቻይና› ነው። እና ምን ቢል ጥሩ ነው? ‹‹እኔንም የሠራኝ ቻይና ነው እንዴ?›› ሆ…ሆ… ይቀራል ብለህ ነው ትንሽ ከቆየን? ማሙሽ…  ይቀራል? አንዱ እኮ ነው በቀደም ለፋሲካ በዓል ገበያ ወጣ ብሎ ለልጆቹ ጫማ ለመግዛት ያስባል፡፡ ከልጆቹ ጋር ሄዶም አንድ ሞል ገብተው ጫማ ሲመርጡ፣ ‹‹አባዬ ይህንን የቬትናም ጫማ ግዛልኝ፣ የቬትናም አሪፍ ነው…›› ይለዋል አንደኛው ልጁ፡፡ አባት ግራ ገብቶት ቆይቶ አሰብ ካደረገ በኋላ፣ ‹‹እውነትህን ነው ልጄ፣ የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም አፈር ያስጋጡት ቬትናሞች ጫማ በጥንካሬው አሪፍ ነው…›› እያለ ሲስቅ፣ ‹‹አባዬ እኔ ፖለቲካ አይደለም ያወራሁት፣ የቬትናሞች ጥራት አለው ማለቴ ነው…›› እያለ አባቱን ለማረም ተፍጨረጨረ፡፡ ይህስ ምን ይባላል? አልተግባብቶም!

ሥራዬን ጨራርሼ ድክም ብሎኝ በጊዜ ገብቼ ልተኛ ስንደፋደፍ ባሻዬ ደወሉልኝ። የት እንዳለሁ ስነግራቸው፣ ‹‹ቶሎ ብለህ ቤት ና!›› አሉኝና ቤታቸው ሄድኩ። ለባብሰው ተዘገጃጅተው ይጠብቁኛል። ‹‹የት ልንሄድ ነው ባሻዬ?›› ስላቸው፣ ‹‹የዛሬ ጊዜ ሰው መጨካከን ከልክ እያለፈ ነው። ኖሮት ባይሰጥህ፣ ባያበድርህ፣ ተርፎት ባያጎርስህ ምናለበት ከወዳጅ ከዘመድ ስትጣላና ስትኳረፍ ምን ሆንክ ብሎ ቢያስታርቅ? ነውር አይደለም ግን?›› አሉኝ አትኩረው እያዩኝ። ምን እንደሚያወሩ ስላልገባኝ፣ ‹‹ደግሞ ማን ተጣላ?›› ብዬ እንዲያብራሩልኝ ስጠይቃቸው፣ በቅርብ የሚያውቋቸው ሊጋቡ የሚጠበቁ ጥንዶች ተኳርፈው እነሱን ሊሸመግሉ እንደምንሄድ ነገሩኝ። ተስማምቼ ሄድን። መቼም ትልቅ ሰው ትልቅ ነው!

ባሻዬ ሰውዬውን አስቀድመው ውጭ ቀጥረው አግኝተውት መክረውና ገስፀውት ሲያበቁ፣ እጮኛው ቤት እንደ ደረስን ጥንዶቹ ምንም ሳይነጋገሩ እንደተያዩ ዘለው ተቃቅፈው ይላቀሱ ጀመር። ‹‹ባሻዬ ምን ጉድ ነው?›› ብለው እኔን ያዩኛል። እኔም እሳቸውን አያለሁ። እሪታና ለቅሶውን እንዲያበርዱት ገስፀን ሁለቱንም ካረጋጋን በኋላ፣ ‹‹ለካ መተያየት ብቻ በቂያችሁ ኖሯል?›› ብለው ባሻዬ በነገር ጠቅ ሲያደርጓቸው ‹‹አይ ባሻዬ! ጓደኛ፣ ወዳጅ፣ ዘመድ የሚባለውንማ አየነው። አንድ ሰው ምን ሆናችሁ ብሎ እንኳ ሳይጠይቀን ይኼው እሱም እሷ ትምጣ፣ እኔም እሱ ይቅርታ ይጠይቀኝ ስል ተለያይተን መቅረታችን ነበር። ምነው ሰው ይህን ያህል የራሱን እንጀራ ብቻ አብሳይ ሆነ?›› አለችን።

ቤት ያፈራውን ቀማምሰንና ቡና ጠጥተን ‹የዓለም የሲሳይ ቤት ያድርገው! ውለዱ ክበዱ! ፍቅራችሁን እስከ መቃብር ያፅናው!› ብለን ስንወጣ ባሻዬ፣ ‹‹አየህ ልጅ አንበርብር! ምን አገባኝ ስንት ነገር እያበላሸ እንዳለ? ስንት ቤተሰብ ሲበተን፣ እህት ወንድም እንደ ደመኛ ሲተያይ፣ አባት እናት ሲለያይ፣ ሁሉ እንደፈለገው ሲጓዝ፣ ኅብረተሰብ ፈር ሲስት ‹ተው ምን ሆናችሁ? ወዴት እየሄድን ነው?› የሚል ሸምጋይ አስታራቂ ማጣት የሚሠራንን? ከሚያቀራርበው የሚያራርቀው፣ ልዩነትን ከሚያጠበው የሚያሰፋው መብዛቱ አያስፈራህም? አይበጀንም አንበርብር! አይበጀንም!›› እያሉኝ፣ ብዙ ስንጫወት አምሽተን ተለያየን። ‹ያስታራቂ ያለህ?› እንበል ወይስ ‹ማን ይሆን ትልቅ ሰው?› ለትውስታ ያህል አነሳሁት እንጂ መልሱን ታውቁታላችሁ። ብቻ ስንትና ስንት እሴቶቻችን ማንቀላፋታቸው ስለሚቆጨኝ ነው። ሰው መሆን እኮ ከምንም ይቀድማል። አይደለም እንዴ? ታዲያ በዚህ ዓይነት ዳግም ውልደት ዳግም ትንሳዔ የሚያስፈልጋቸው ማኅበራዊ እሴቶቻችንን ቁጠሩ እስቲ። እጅ አልገባም እንጂ መቁጠር መቼ አቃተን ያለው ማን ነበር? ረሳሁት!

ወደ ምናዘወትራት ግሮሰሪ ጎራ ብለን እኔና የባሻዬ ልጅ አንድ አንድ ይዘናል። ሰው ከፍላት ስክሪን ስልኩ፣ ወደ ፍላት ስክሪኑ ቴሌቪዥን ዓይኖቹን እያመላለሰ ወሬ ቀዝቅዟል። ሰው የናፈቀው አንድ ሰካራም፣ ‹‹ይኼ ኳስ አያልቅም እንዴ?›› ይላል። ‹‹ገና መቼ ተጀመረ?›› ይላል ከጎኑ የተቀመጠው። ‹‹አይሰለቻችሁም?›› ብሎ መልሶ ይጠይቃል። ‹‹የሚጫወቱልን ሳይሰለቻቸው እኛን ምን ብሎ ይሰለቸናል?›› ይላል ፊት ለፊቱ አረንጓዴ ካፖርት በቢጫ የአንገት ልብስ አጣጥሞ የለበሰ ጎልማሳ። ‹‹ኢትዮጵያ አለችበት እንዴ?›› ሲል፣ ‹‹አቦ ዝም በል ኳስ እንይበት…›› ብሎ አንዱ ተቆጣው። ‹‹እሺ ኤርትራስ?›› ሲል አላስችል ያላቸው በሳቅ ፈረሱ። ‹‹ፕሪሚየር ሊጉ አገር ያስተናግዳል እንዴ? ወይ ወዲህና ወዲያ? አሁን ገና ስለኳስ አወራህ…›› ቢለው አንዱ ሞቅ ያለው ዋዘኛው በተሳሰረ አፉ፣ ‹‹የምሬን ነው፣ የራሳችንን ጨዋታ ሳንጨርስ የሰው ግጥሚያ ስናይ ይገርመኛል…›› አለ፡፡ ያ ጎልማሳ፣ ‹‹ምን አባታችን እናድርግ ወዳጄ። የእኛ ንትርክና ግጭት የሰዓት ገደብ የለው፣ ዕረፍት የለው፣ ውጥረት የለው፣ ዳኛ የለው፣ ምን የለው፣ ምን የለው። ቢያንስ እነሱ ቢታገሉም ቢራገጡም ጊዜ ይለያሉ…›› ብሎ ቴሌቪዥኑን ሲጠቁመው፣ ‹‹ባልከው ቅደም ተከተል ሥርዓት አስከባሪ ባይኖረንም አራጋቢ ስላለን አይዞህ…›› ቢል አሁንም ግሮሰሪዋ ሳቅ በሳቅ ሆነች። የገባውም ያልገባውም ሳቀ። ሞኝ ሳይገባው ይስቃል ቢባልም እኛም ሲስቁ ዓይተን ሳቅን። እስኪ እናንተም አንዴ ሳቅ፣ ፈገግ በሉ፡፡ መልካም የትንሳዔ በዓል! መልካም ሰንበት!     

Latest Posts

- Advertisement -

ወቅታዊ ፅሑፎች

ትኩስ ዜናዎች ለማግኘት