በዓለም አቀፍ ደረጃ አገሮች ያላቸውን በኢንተርኔት የሚፈጸም የመረጃ ጥሰትን የተመለከተ ጥናት፣ ኢትዮጵያ ከዓለምና ከአፍሪካ አገሮች ዝቅተኛ የመረጃ ምንተፋ እንደሚደርስባት አመላከተ፡፡
ሰርፍ ሻርክ የተባለ የሳይበር ደኅንነት ተቋም አገሮች በሚደርስባቸው የመረጃ ምንተፋ ያላቸውን ደረጃ ለመለየት ባደረገው ጥናት፣ በኢትዮጵያ ከ100 የኢሜይል አካውንቶች ውስጥ የመረጃ ምንተፋ የሚያጋጥመው 0.5 ያህሉ ብቻ መሆኑን እንዳረጋገጠ አስታውቋል፡፡
በዚህ ጥናት ላይ ጎረቤት አገር ሱዳን በመረጃ ምንተፋ ከአፍሪካ አገሮች በቀዳሚነት የተቀመጠች ሲሆን፣ ከ100 የኢሜይል አካውንቶች ውስጥ 70 ያህሉ የመረጃ ምንተፋ ያጋጥማቸዋል ተብሏል፡፡ እንደ አኅጉር ደግሞ አፍሪካ ዝቅተኛ የመረጃ ምንተፋን ታስተናግዳለች፡፡ እስያና ደቡብ አሜሪካ አፍሪካን ይከተላሉ፡፡
ምንም እንኳ በዓለም አቀፉ ተቋም የተደረገው ጥናት በኢንተርኔት በሚፈጸም የመረጃ ምንተፋ ኢትዮጵያ ዝቅተኛ ደረጃ ላይ ብትቀመጥም፣ የኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት (ኢንሳ) አስተዳደር መረጃ በ2014 ዓ.ም. የተፈጸሙ የሳይበር ጥቃት ሙከራዎች በአራት እጥፍ መጨመራቸውን ይናገራል፡፡
ሪፖርተር ያነጋገራቸው በኢንሳ የሳይበር ሴኪዩሪቲ ባለሙያ አቶ ሰብለ ወይን፣ ጥናቱ ከሳይበር ጥቃቶች መካከል አንዱ በሆነው የመረጃ ምንተፋ ላይ ብቻ ያተኮረ በመሆኑ በአገሪቱ ውስጥ ያለውን የሳይበር ጥቃት ሁኔታ ሊወክል እንደማይችል አስረድተዋል፡፡ በጥናቱ የተዳሰሰውን የመረጃ ምንተፋ ጥቃት በተመለከተም በአገሪቱ ያሉት የኢሜይል ተጠቃሚ ሰዎች ብዛት ባለመለየቱ፣ ኢንሳ በጥናቱ ላይ በተጠቀሰው ልክ ያጠናቀረው ዳታ እንደሌለ ገልጸዋል፡፡ በአገር ደረጃ የሚደርሱ የሳይበር ጥቃቶች በየዓመቱ እየጨመሩ መምጣታቸውን አክለዋል፡፡
የኢንሳ መረጃ እንደሚያሳየው፣ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከፍተኛ ጉዳት ሊያደርሱ የሚችሉ 5,856 የሳይበር ጥቃት ሙከራዎች ተደርገው 97.7 በመቶዎቹ ምላሽ ተሰጥቷቸዋል፡፡
የተሰነዘሩት ጥቃቶች የጂኦፖለቲካል ፍላጎት ባላቸው አገሮች የተፈጸሙ ስለመሆናቸው የገለጸው ኢንሳ፣ ከታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴው ግድብ፣ ስድስተኛው አገራዊ ምርጫና ከሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት ጋር የሚያያዙ መሆናቸውን አስታውቋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የፋይናንስ ተቋማት፣ ቁልፍ መሠረተ ልማቶች፣ የመንግሥትና መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማት ድረ ገጾችና የመገናኛ ብዙኃንም የጥቃቱ ዒላማ መሆናቸው ተጠቅሷል፡፡
እንደ ተቋሙ መረጃ፣ ከእነዚህ የሳይበር ጥቃቶች ውስጥ ከፍተኛውን ቁጥር የሚይዘው የድረ ገጽ ጥቃት ነው፡፡ አጥፊ የማልዌር ጥቃት፣ የመሠረተ ልማት አገልግሎት ማቋረጥና የኦንላይን ማጭበርበር ደግሞ በተከታይነት ተቀምጠዋል፡፡
የመረጃ ምንተፋ ላይ ጥናት የደረገው የሰርፍ ሻርክ መረጃ ከሁለት የኢንተርኔት ተጠቃሚዎች ውስጥ የአንዱ መረጃ ከሚመነተፍበት ሰሜን አሜሪካ አንፃር በአፍሪካ የሚደርሰው ጥቃት ዝቅተኛ ነው ይላል፡፡ በአፍሪካ አገሮች ውስጥ በሚፈጸሙ የሳይበር ጥቃቶች ብዛት ከዓለም ቀዳሚ አሥር አገሮች ውስጥ የተካተተችው ደቡብ አፍሪካ ብቻ ነች፡፡