በአካል ጉዳተኞች ጉዳይ የሚወጡ ሕጎች ሙሉ በሙሉ ተደራሽ እንዳልሆኑና ብዙ ክፍተቶች እንዳሉባቸው፣ የኢትዮጵያ የአካል ጉዳተኞች ማኅበራት ፌዴሬሽን አስታወቀ፡፡
የሕንፃና የሥራ ሥምሪት አዋጅን ጨምሮ በርካታ ሕጎች ለአካል ጉዳተኞች ሳይሆን ለጉዳት አልባዎች የተዘጋጀ እንደሚመስል የተገለጸው፣ ማክሰኞ ሚያዝያ 18 ቀን 2014 ዓ.ም. የ25ኛ ዓመት የኢትዮጵያ የአካል ጉዳተኞች ማኅበራት ፌዴሬሽን የምሥረታ በዓል ላይ ነው፡፡
የኢትዮጵያ አካል ጉዳተኞች ማኅበራት ፌዴሬሽን ዋና ዳይሬክተር አቶ ዓባይነህ ጉጆ እንደተናገሩት፣ የሕንፃና የሥራ ሥምሪት አዋጆች የራሳቸው ችግሮች አሉባቸው፡፡
ሕጎቹ ከራሳቸው ክፍተቶች በተጨማሪ ተፈጻሚነት ላይም ቢሆን ውስብስብ ችግሮች እንዳሉባቸው ተገልጿል፡፡ አንድ ሕንፃ ሲገነባ ከሦስተኛ ፎቅ በላይ አሳንሰር (ሊፍት) እንደሚያስፈልግ ሕጉ እንደሚያስገድድ የገለጹት አቶ ዓባይነህ፣ እስከ ሦስተኛ ፎቅ ድረስ እንዴት ይጓዛሉ የሚለውን ያልፈተሸ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ሕጎችን እንኳን ተፈጻሚ የሚያደርጉ ተቋማት ጥቂቶች መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
አካል ጉዳተኞችን ይጠቅማሉ ተብለው የሚወጡ በርካታ ሕጎች በክፍተታቸውና በተደራሽነት ጉድለት ሳቢያ የሉም የሚባሉበት ደረጃ መድረሳቸውን አቶ ዓባይነህ ገልጸዋል፡፡
ለአካል ጉዳተኞች ምቹ ሁኔታን ለመፍጠር መሠረት የተጣለባቸውን የተሻሉ ሁኔታዎች ያመጣል በሚል ተስፋ በመሰነቃቸው፣ 25ኛ የምሥረታ በዓላቸውን እያከበሩ እንደሚገኙ አስረድተዋል፡፡
የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች አዋጅ መቀየሩ ለአካል ጉዳተኞች ትልቅ ለውጥ መሆኑን የገለጹት ዋና ዳይሬክተሩ፣ ከመጀመሪያው ጊዜ አንስተው ተሳታፊ እንደነበሩ አስታውሰዋል፡፡
‹‹ያለ እኛ ስለእኛ ምንም መባል የለበትም›› በማለት በሲቪል ማኅበረሰብ አዋጅ ስለአካል ጉዳተኞች በሚወጡ ሕግና መመርያዎች በመሪነት ተሳታፊ እንደነበሩ ገልጸዋል፡፡
በአጠቃላይ ለአካል ጉዳተኞች ጉዳይ የሚወጡ ሕጎችን ተደራሽነትና ተፈጻሚነት በተመለከተ፣ ከትናንትናው የዛሬው የተሻለ መሆኑን፣ ነገር ግን ብዙ የሚቀሩና መሻሻል ያለባቸው አሠራሮች እንዳሉ ጠቁመዋል፡፡
ከዚህ በዘለለ የመንግሥት ተቋማት በዕቅዳቸው፣ በዓላማቸውና በተግባራቸው የአካል ጉዳተኞችን ጉዳይ ማካተት ካልቻሉ የተሻለች ኢትዮጵያን ለመገንባት እንደማይቻል ዋና ዳይሬክተሩ ተናግረዋል፡፡
በምክንያትነት ያቀረቡት ከ20 ሚሊዮን ይበልጣሉ ተብለው የሚገመቱ የኅብረተሰብ ክፍሎች አካል ጉዳተኞች መሆናቸውን፣ የልማቱ ተሳታፊ በማድረግ አገር ከእነሱ ማግኘት ያለባትን ጥቅም እንድታገኝ ማድረግ እንደሚያስፈልግ አሳስበዋል፡፡
የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስትሯ ኤርጎጌ ተስፋዬ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ ብዙ ችግሮችን ሊፈታ የሚችል አዲስ የተጠቃለለ ሕግ ከረቂቁ ጀምሮ ፌዴሬሽኑ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ተናግረዋል፡፡
በመራቀቅ ላይ ያለው ሕግ በጣም አከራካሪ ነገሮች እንዳሉት፣ ነገር ግን ኢትዮጵያ የፈረመቻቸውን ዓለም አቀፍ ሕጎች አክብራ እንድትገኝ የሚያስችል መሆኑን ሚኒስትሯ አስረድተዋል፡፡
በረቂቅ ደረጃ የሚገኝ ሕግ መሆኑን የጠቆሙት ኤርጎጌ (ዶ/ር)፣ ተጠናቅቆ ለሚመለከታቸው አካላት እንደሚሰጥ ተናግረዋል፡፡