Friday, September 22, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ዜናባለድርሻ አካላት የሚሳተፉበት የደመወዝ ቦርድ እንዲያቋቁም ተጠየቀ

ባለድርሻ አካላት የሚሳተፉበት የደመወዝ ቦርድ እንዲያቋቁም ተጠየቀ

ቀን:

የኢትዮጵያ ሠራተኛ ማኅበራት ኮንፌዴሬሽን (ኢሰማኮ) እና ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን መንግሥት ባለድርሻ አካላት የሚሳተፉበትን የደመወዝ ቦርድ በአስቸኳይ እንዲያቋቁም ጠየቁ፡፡

በመንግሥት የተቋቋመው አካል የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ከሰሞኑ ባወጣው መግለጫ ላይ እንዳስታወቀው፣ በ2011 ዓ.ም. መባቻ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በፀደቀው የአሠሪና ሠራተኛ አዋጅ ቁጥር 1156/2011 ድንጋጌ የደመወዝ ቦርድ በአስቸኳይ እንዲቋቋም መጠየቁ ይታወሳል፡፡

በአዋጁ ክፍል ሦስት ምዕራፍ ሁለት አንቀፅ 55 ላይ የአገሪቱ የኢኮኖሚ ዕድገት፣ የሥራ ገበያ ሁኔታና የመሳሰሉትን እያስጠና ዝቅተኛ ደመወዝ የሚወስን የመንግሥት፣ የአሠሪና ሠራተኛ ተወካዮች እንዲሁም ሌሎች ባለድርሻ አካላት የሚሳተፉበት የደመወዝ ቦርድ ስለሚቋቋምበትና ተግባርና ኃላፊነቱ ስለሚወሰንበት ሁኔታ በሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ይደነገጋል፡፡ 

የኢትዮጵያ ሠራተኛ ማኅበራት ኮንፌዴሬሽን (ኢሰማኮ) ፕሬዚዳንት አቶ ካሳሁን ፎሎ ለሪፖርተር እንዳስታወቁት፣ አገር አቀፍ ዝቅተኛ የደመወዝ ወለል ስንት መሆን አለበት? የሚለውን ከውጭ ባለሙያ ቀጥሮ አስጠንቷል፡፡ ይህንን ተከትሎ በዚህ ወቅት መንግሥት ከመቼውም ጊዜ በላይ ወደ ተግባር እንዲያውለው ጥያቄ የቀረበለት የደመወዝ ቦርድ መቋቋም ይፋ ሲደረግ፣ ኢሰማኮ ያስጠናውን ጥናት ለድርድር ይፋ እንደሚያደርገው ተናግረዋል፡፡

በአሠሪውም ሆነ በራሱ በመንግሥት ዝቅተኛ የደመወዝ ወለል አስመልክቶ የሚዘጋጁት ጥናቶች ሣይንሳዊ ቀመርን የተከተሉ መሆናቸው የሚሰመርበት እንደሆነ የተናገሩት አቶ ካሳሁን፣ ኢሰማኮ ግን ሠራተኛውን በተመለከተ ለድርድር ሲቀርብ የተጠና ነገር ይዞ መቅረብ አለበት የሚለውን ለመመለስ የራሱን የጥናት ዝግጅት እንዳደረገ አስታውቀዋል፡፡

ኮንፌዴሬሽኑ ያስጠናው የዝቅተኛ የደመወዝ ወለል የተመለከተው ጥናት በዚህ ወቅት እንደተጠናቀቀ የተገለጸ ሲሆን፣ ነገር ግን የቦርዱን መቋቋም እየተጠባበቀ ስለሚገኝ በዚህ ወቅት ይፋ ከማድረግ እንደተቆጠበ አቶ ካሳሁን አስታውቋል፡፡

የሠራተኛውን መብት አስመልክቶ ከሰሞኑ በተለያዩ ተቋማት የሚስተጋቡት መግለጫዎች አሳማኝ፣ ትክክለኛና ወቅታዊ ስለሆነ ስለሰብዓዊ መብት የሚያስቡ ሰዎች ወደ ፊት የሚደግፉት እንደሆነ ፕሬዚዳንቱ ተናግረዋል፡፡

ኢሰማኮ በቅርቡ ባከናወነው ጠቅላላ ጉባዔ ላይ ባወጣው የአቋም መግለጫ ያስቀመጣቸው ጉዳዮች ተግባራዊ እንዲሆኑ፣ በተለይ ዝቅተኛ የደመወዝ ወለል በሚመለከት ክትትል እያደረገ እንደሚገኝ አቶ ካሳሁን ገልጸዋል፡፡ ዝቅተኛ የደመወዝ ወለል እስኪወጣ ድረስ ግፊት እንደሚደረግና ወደ ኋላ የሚባልበት ነገር እንደሌለ የተገለጸ ሲሆን፣ የኑሮ ውድነቱ ሰውን ከመቼውም ጊዜ በላይ እየጎዳው መገኘቱ መሠረታዊውና አንገብጋቢው ምክንያት እንደሆነ ተነግሯል፡፡

ለአብነት ኬንያ በሳምንቱ መጀመሪያ በተከበረው የዓለም አቀፍ የላብ አደሮች ቀን ከዚህ ቀደም በሥራ ላይ የነበረውን ዝቅተኛ የደመወዝ ወለል የኑሮ ውድነትን ከግምት ውስጥ በመክተት፣ የኬንያው ፕሬዚዳንት አደባባይ ላይ ተገኝተው ዝቅተኛ የደመወዝ ወለሉን በአዋጅ በ12 በመቶ እንዲጨምር እንዳደረጉ አቶ ካሳሁን አስታውሰዋል፡፡

አንድ ሠራተኛ በወር እንድ ሺሕ ብር አግኝቶ በሕይወት መገኘቱ በራሱ አስገራሚ እንደሆነ ያስታወቁት ፕሬዚዳንቱ፣ ከዚህ አንፃር በኢትዮጵያ ዝቅተኛ የደመወዝ ወለል መወሰን እንዳለበት ተናግረዋል፡፡

ኮንፌዴሬሽኑ መንግሥትን እየጠየቀ የሚገኘው ያወጣውን ሕግ ተግባራዊ እንዲደርግ ነው ያሉት የኢሰማኮ ፕሬዚዳንት፣ መንግሥትም ይህንን ተግባራዊ አላደርግም የሚል ዕሳቤ እንደማይኖረው ዕምነታቸውን ገልጸዋል፡፡

በሌላ በኩል ሚያዚያ 23 ቀን 2014 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ከተማ ደረጃ የዓለም የላብ አደሮች ቀን (ሜይዴይ) ሲከበር ንግግር ያደረጉት የሥራና ክህሎት ሚኒስትሯ ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል፣ መንግሥት የሠራተኞችን ዝቅተኛ የደመወዝ ወለል ለመወሰን የገባውን ቃል አያጥፍም ብለዋል፡፡ ነገር ግን ጉዳዩ በጥልቅ ጥናት ታይቶ ሊሠራ የሚገባው ስለሆነ ጥናቶች እየተከናወኑ እንደሆኑ ጨምረው ተናግረዋል፡፡

የተሻሻለው የሠራተኛ አዋጅ የሠራተኛና ሲቪክ ማኅበራትን ያካተተ የደመወዝ ቦርድ እንዲቋቋም የሚጠይቅ ሲሆን፣ ቦርዱ በጥናት ላይ ተመሥርቶ ዝቅተኛ የሠራተኛ ደመወዝን የመወሰን ሥልጣን አለው። ኮሚሽኑ ባወጣው መግለጫ መንግሥት የሠራተኛ ዝቅተኛ የደመወዝ ወለልን በአስቸኳይ እንዲወስን የጠየቀ ሲሆን፣ የደመወዝ ወለል ረቂቅ ለሚኒስትሮች ምክር ቤት መቅረቡንም አያይዞ ገልጿል።

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

የዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ባለሙያዎች ኮሚሽን ሪፖርት ምን ይዟል?

ለአሜሪካ ድምፅ አማርኛ ዝግጅት የስልክ አስተያየት የሰጡ አንድ የደንበጫ...

መንግሥት በአማራ ክልል ለወደሙ የአበባ እርሻዎች ድጋፍ እንዲያደርግ ተጠየቀ

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በአማራ ክልል የተፈጠረው ግጭትና አለመረጋጋት በቢዝነስ...

አምናና ዘንድሮ!

እነሆ መስከረም ጠብቶ በአዲስ መንፈስ ተሞልተን መንገድ ጀምረናል። ‹‹አዲስ...