የንግድና ቀጣናዎች ትስስር ሚኒስቴር ጥራጥሬና የቅባት እህሎችን ወደ ውጭ የሚልኩ ነጋዴዎች፣ ሚኒስቴሩ በጽሑፍ ባሳወቃቸው በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ መላክ እንዳለባቸው የሚያስገድዱ ሁለት መመርያዎችን አሻሽሎ ተግባራዊ አደገረ፡፡ ሚኒስቴሩ ባለፈው ሳምንት በ2008 ዓ.ም. ወጥተው የነበሩ ሰሊጥና ነጭ ቦለቄ፣ እንዲሁም ሌሎች የጥራጥሬ እህሎች የግብይት አፈጻጸም መመርያዎችን አሻሽሎ ተግባራዊ አድርጓል።
በተሻሻሉት መመርያዎች ውስጥ የተጨመሩት ሁለት ንዑስ አንቀጾች ሲሆኑ፣ እነሱም ሰሊጥና ነጭ ቦሎቄ፣ እንዲሁም የተለያዩ ጥራጥሬ ምርቶችን ወደ ውጭ የሚልኩ ነጋዴዎች፣ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ በጽሑፍ ባስታወቃቸው በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ልከው እንዲሸጡ የሚያስገድድ ነው።
ምርቶቹ የአንድ የምርት ዘመን ባያልፍባቸውምና በተለያዩ ይዘት መጠን ቢሆኑም፣ ይዞ መቆየት የማይቻል መሆኑንም የተሻሻለው መመርያ ይደነግጋል።
የንግድ ሚኒስቴር በያዝነው ወር መጀመርያ ላይ እንዳስታወቀው፣ ከሩብ ሚሊዮን ቶን በላይ መጠን ያላቸውን የቅባት እህሎችና የተለያዩ ጥራጥሬ እህሎችን በተለያዩ መጋዘኖች ተከማችተው የያዘ መሆኑን ጠቀሶ፣ ነጋዴዎችም ከዚህ ተግባራቸው ተቆጥበው ወደ ውጭ እንዲልኩ አስጠንቅቆ ነበር።
በክምችት ተይዘው የነበሩት እህሎችም በአራት አካባቢዎች ማለትም በአዳማ፣ በአቃቂ ቃሊቲ፣ በቡራዩና በገላን ከተሞች ሲሆን፣ ከእህሎቹ ውስጥ የቅባት እህል ከፍተኛው ነበር።
በመንግሥት በኩል ቁጥጥር መብዛቱ አገሪቱ ያለችበት የውጭ ምንዛሪ እጥረት እንደ ምክንያት የሚጠቀስ ሲሆን፣ በሚኒስቴሩ የግብርና ምርቶች የውጪ ንግድ ግብይት ዳይሬክተሩ አቶ መስፍን አበበም ይህንኑ ያረጋግጣሉ። እንደ አቶ መስፍን ገለጻ አንዳንድ ነጋዴዎች አገሪቱ ማግኘት ያለባትን የውጭ ምንዛሪ እንዳታገኝ በሚያደርግ ሁኔታ ላይ የተሰማሩ ሲሆን ከዚህም እንዲቆጠቡ አሳስበዋል።
‹‹በዋነኝነት ግን የጥራጥሬ ምርቶች በክምችት ላይ ሲሆኑ፣ ወደ መበላሸትና የጥራት ጉድለት ይሄዳሉ፤›› ሲሉም፣ የምርቶችን ከገበያ አሽሽቶ ማከማቸት ያለውን ጉዳት አቶ መስፍን ለሪፖርተር ገልጸዋል።
የግብርና ምርቶች በአገሪቱ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ምንጭ ሲሆኑ፣ በመጠናቀቅ ላይ ባለው በጀት ዓመትም በዘጠኝ ወራት ውስጥ ብቻ ጥራጥሬዎችና የቅባት እህሎችን ጨምሮ፣ አጠቃላይ የግብርና ምርቶች ከሁለት ቢሊዮን ዶላር በላይ ገቢ አስገኝተዋል። ከእነዚህም ቡና ግማሽ የሚሆነውን ይይዛል።
ባለፈው ዓመት ከውጭ ንግድ ተገኝቶ ከነበረውም አጠቃላይ 3.6 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ውስጥ የቅባት እህል 9.45 በመቶውን ሲሸፍን፣ ሌሎች ጥራጥሬዎች ደግሞ 6.11 በመቶውን ይሽፍኑ ነበር። ቡና ከዓምና የውጭ ንግድ ገቢ 25 ከመቶውን ይሸፍን ነበር።
ሚኒስቴሩ ከዚህ በፊትም ተመሳሳይ ማስጠንቀቂያዎችን አውጥቶ የነበረ ሲሆን፣ አሁን ግን መመርያ በማሻሻል ምርቶች ወደ ውጭ የሚላኩበትን መንገድ ወጥኗል። የተለያዩ አገሮች ላኪ ነጋዴዎችም ከባለፈው ጥር ወር ጀምሮ በብሔራዊ ባንክ ተግባራዊ ሆኖ በነበረው የውጭ ምንዛሪ አወሳሰን ፖሊሲ ላይ ቅሬታቸውን ሲያቀርቡ ነበር።
በዚህ ፖሊሲ ምክንያት ላኪዎች ከሚያገኙት የውጭ ምንዛሪ ውስጥ 20 በመቶውን ብቻ የሚጠቀሙበት አብዛኛ ላኪ ነጋዴዎችም፣ የውጭ ምንዛሪዎችን በመፈለግ ምርቶችን በከፍተኛ ዋጋ በአገር ውስጥ ምንዛሪ እንደሚገዙ ይታወቃል።