የፀጥታ ችግር የዘርፉ ዋነኛ ፈተና መሆኑ ተገልጿል
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች በማዕድን ኩባንያዎች የሚደረግ የማዕድን ፍለጋና ቁፋሮ፣ የቀጣዩን ትውልድ ሕይወት አደጋ ላይ የሚጥል እንዳይሆን አሳሰበ፡፡
ፓርላማው ማክሰኞ ግንቦት 16 ቀን 2014 ዓ.ም. የማዕድን ሚኒስቴርን የ2014 ዓ.ም. የአሥር ወራት ዕቅድ አፈጻጸም፣ 238 የምክር ቤት አባላት በተገኙበት ገምግሟል፡፡
የምክር ቤቱ የኢንዱስትሪና የማዕድን ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ዋና ሰብሳቢ አማረች በካሎ (ዶ/ር)፣ የዛሬው ትውልድ ማዕድን ሲያመርት በነገው ትውልድ ላይ ጫና እያደረሰ አለመሆኑ መረጋገጥ አለበት ብለዋል፡፡ የማያቋርጥ ክትትል በማድረግ፣ ዘለቄታዊ ስትራቴጂ በማዘጋጀትና ለኩባንያዎች ፈቃድ ሲሰጥም ሆነ ሲታደስ በመሥፈርቱ መሠረት ኩባንያዎቹ እየተንቀሳቀሱ መሆናቸውን ማረጋገጥ ይገባል ሲሉ አሳስበዋል፡፡
በተለይ ከአካባቢና ውኃ ብክለት፣ ከመኖሪያ መፈናቀል፣ ለሰዎች አኗኗር አመቺ ያልሆኑ የመሬት ቁፋሮዎች በተገቢው ሁኔታ ጥብቅ ክትትል እንዲደረግባቸውና ለዚህም ይረዳ ዘንድ አልሚ ኩባንያዎች የሚመሩበት ግልጽ የሆነ አገራዊ ፖሊሲ እንዲዘጋጅ ጠይቀዋል፡፡
ፖሊሲና የሕግ ማዕቀፍ ከማዘጋጀት ባላፈ ኩባንያዎች በማዕድን ልማት ሲሰማሩ፣ ከአካባቢው ነዋሪ ጋር በመወያየትና የሕዝቡን ተጠቃሚነት በማረጋገጥ፣ በዘርፉ ረዥም ርቀት ሊያስኬድ የሚያሰችል ሥራ እንዲያከናውኑ የማዕድን ሚኒስቴርን አሳስበዋል፡፡
ባለፉት አሥር ወራት በባህላዊ አምራቾችና በኩባንያዎች አማካይነት የተመረቱ 6,947 ኪ.ግ ወርቅ፣ 79 ቶን ታንታለም፣ ከ10 ሺሕ ኪ.ግ በላይ ጥሬና 120 ኪ.ግ እሴት የተጨመረበት ኦፓል፣ 2,000 ኪሎ ግራም የጌጣጌጥ ማዕድናት፣ 7,300 ቶን አዳዲስ የኢንዱስትሪ ማዕድናት ለአገር ውስጥና ለውጭ ገበያ ቀርበው፣ 458 ሚሊዮን ዶላር መገኘቱን የማዕድን ሚኒስትሩ ታከለ ኡማ (ኢንጂነር) በሪፖርታቸው አስረድተዋል፡፡
የማዕድን ሚኒስቴር በበጀት ዓመቱ በዘጠኝ ወራት ውስጥ ከማዕድናትና ከተፈጥሮ ጋዝ ምርት ሽያጭ በአጠቃላይ 996 ሚሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሪ ገቢ ለማግኘት አቅዶ የነበረ ቢሆንም፣ የተፈጥሮ ጋዝ ምርት በታቀደው ጊዜ ወደ ምርት ባለመግባቱ 458 ሚሊዮን ዶላር (የዕቅዱን 46 በመቶ) ብቻ እንዳሳካ ተገልጿል፡፡
በአሥር ወራት ውስጥ ለ39 አዳዲስ የማዕድን ምርመራና ለ16 ለማምረት ለሚሰማሩ ኩባንያዎች ፈቃድ የተሰጠ መሆኑን፣ ከእነዚህ መካከል 15 በምርመራና ዘጠኝ በምርት ላይ የሚሳተፉ የአገር ውስጥ ባለሀብቶች እንደሚገኙበት ታከለ (ኢንጂነር) ተናግረዋል፡፡
ከውጭ የሚገቡ የኢንዱስትሪ ማዕድናት ውጤቶችና ጥሬ ዕቃዎችን በአገር ውስጥ ለመተካት እየተሠራ መሆኑን የገለጹት ሚኒስትሩ፣ የድንጋይ ከሰል፣ ብረት፣ የማዳበሪያና የግንባታ ግብዓት ማዕድናት በልዩ ሁኔታ ለማልማት በፕሮጀክት ደረጃ የማደራጀት ሥራ እየተከናወነ መሆኑን፣ በቀጣይ ዓመታት ሁሉንም ውጤቶች በሒደት ከውጭ ማስገባት እንደሚቆም ገልጸዋል፡፡
ባለፉት አሥር ወራት ስምንት ሚሊዮን ቶን የሲሚንቶ ምርት ወደ ገበያ ለማቅረብ ታቅዶ 4.8 ሚሊዮን (58) በመቶ ብቻ በፋብሪካዎች እንደተመረተ፣ ለአፈጻጸሙ ዝቅተኛ መሆኑን በዋነኝነት የፀጥታ ችግር፣ የኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማሳደሩን ሚኒስትሩ አስረድተዋል፡፡
በ14 የተለያዩ የማዕድን ማውጫ ቦታዎች ላይ የፀጥታ ሥጋት ችግሮችን ለመፍታት ከመከላከያ ሚኒስቴር፣ ከፌዴራል ፖሊስ፣ ከመረጃ ደኅንነት መረብ ኤጀንሲና ከአርተፊሻል ኢንተለጀንስ ተቋማት ጋር ውይይት በማድረግ የማዕድን ፖሊስ ለማቋቋም የመግባቢያ ስምምነት በመፈራረም ወደ ሥራ መገባቱ በሪፖርታቸው ተጠቁሟል፡፡