በእስር ላይ የነበሩት የቀድሞ የመከላከያ ኮሙዩኒኬሽንና ኤሌክትሮኒክስ ሳይቨር መምርያ ኃላፊ ሜጀር ጀነራል ገብረ መድኅን ፍቃዱ (ወዲ ነጮ) ከትናንት በስቲያ ሚያዝያ 24 ቀን 2014 ዓ.ም. ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ፡፡
ሜጀር ጀነራል ገብረ መድኅን ፍቃዱ ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም. በሰሜን ዕዝ ላይ ከተፈጸመ ግድያ ጋር በተያያዘ በቁጥጥር ሥር ውለው በተመሠረተባቸው የወንጀል ክስ በመከራከር ላይ ነበሩ፡፡
የፌደራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ (አሁን ፍትሕ ሚኒስቴር) ኃላፊውን ከሌሎች ግለሰቦች ጋር በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ሦስተኛ የፀረ ሽብርና የሕገ መንግሥታዊ ጉዳዮች ወንጀል ችሎት ክስ መሥርቶ ምስክሮች እያሰማ ነበር፡፡
ተከሳሹ ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም. በሰሜን ዕዝ ላይ ጥቃት ሲፈጽም መገናኛ ሬዲዮ ስለማቋረጣቸው ዓቃቤ ሕግ ቀደም ባሉ ሁለት ቀጠሮዎች ካሰማቸው ምስክሮች በተጨማሪ ለትናንት ሚያዝያ 25 ቀን 2014 ዓ.ም5 ቀጠሮ ተሰጥቶ የነበር ቢሆንም፣ ሜጀር ጀነራል ገብረ መድኅን ፍቃዱ በድንገት ማረፋቸው ታውቋል፡፡
ጀነራሉ ቤተሰቦቻቸው በማረሚያ ቤት ሄደው እንደተገናኙና በመነጋገር ላይ እያሉ ተዝለፍልፈው ሲወድቁ ከመታየታቸው በስተቀር በምን ምክንያት ሕይወታቸው እንዳለፈ ሪፖርተር ለማጣራት ያደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡
ባለትዳርና የአራት ልጆች አባት እንደነበሩ የተገለጸው ሜጀር ጀነራል ገብረ መድኅን የቀብር ሥነ ሥርዓት ዛሬ ሚያዝያ 26 ቀን 2014 ዓ.ም. እንደሚፈጸም ታውቋል፡፡