የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በየክፍለ ከተማው ደረጃቸውን የጠበቁ የስፖርት ማዘውተሪያ ጂምናዚየሞችን እያስገነባ መሆኑን ቢያስታውቅም፣ በጂምናዚየሞቹ ግንባታ ላይ ጥያቄዎች እየተነሱ ነው፡፡
የአዲስ አበባ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ በጉለሌና በልደታ ክፍላተ ከተማ ጂምናዚየሞቹ መገንባታቸውንና በአራዳ፣ በቦሌና በኮልፌ ክፍላተ ከተሞች ለመገንባት ዝግጅት መጀመሩን አስታውቋል፡፡ በከተማው አስተዳደር ዋና ሕንፃ ላይም ተመሳሳይ የስፖርት ማዘውተሪያ ጂምናዚየም ለመገንባት መታቀዱን ቢሮው ይፋ አድርጓል፡፡
የአዲስ አበባ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ የስፖርት ማዘውተሪያ ጂምናዚየሞች ግንባታ በዕቅድ ተይዞ እየተሠራ መሆኑን፣ ፕሮጀክቱም ከአገሪቱ የስፖርት ፖሊሲ ጋር የተጣጣመ መሆኑንና በሥራ ቦታዎች ላይ ምቹ የሥራ ሁኔታ ለመፍጠር ታስቦ የተጀመረ መሆኑን ገልጿል፡፡
ነገር ግን የልደታ ክፍለ ከተማ የስፖርት ማዘውተሪያ ጂምናዚየም ግንባታ ዜና በኦፊሴላዊ የፌስቡክ ገጹ ላይ ከወጣ በኋላ፣ በርካታ ቅሬታዎች ቀርበዋል፡፡ ጂምናዚየም ከመገንባት ለሕዝብ መሠረታዊ አገልግሎቶችን ማቅረብና የነዋሪዎችን ችግር መፍታት አይቀድምም ወይ? ሲሉ በርካቶች በፕሮጀክቱ ላይ ቅሬታ አሰምተዋል፡፡
በሌላ በኩልም ለ42 ሠራተኞችና አመራሮች የልደታ ክፍለ ከተማ 5.7 ሚሊዮን ብር ወጪ በማድረግ ጂምናዚየም መገንባቱ ቅንጦትና አባካኝነት ነው በሚል ተተችቷል፡፡
ከዚሁ ጎን ለጎንም አገሪቱ ቅድሚያ ልትሰጣቸው የሚገቡ ብዙ አሳሳቢ ችግሮች እያሉ፣ በአዲስ አበባ ግን በየክፍለ ከተማው የጂምናዚየም ግንባታ መጀመር ያልተገባ ሥራ ነው ተብሎ ተብጠልጥሏል፡፡
ሌሎች በበኩላቸው የኑሮ ውድነትና የዋጋ ግሽበት አንገብጋቢ በሆነበት ከተማ፣ የነዋሪውን ችግር ሳይሆን ለወረዳ አመራሮችና ሠራተኞች ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር ጥረት ማድረግ ተገቢነት እንደሌለውም በጉዳዩ ላይ ቅሬታዎች አቅርበዋል፡፡
ይሁን እንጂ ይህን መሰሉ ቅሬታና ትችት አግባብነት እንደሌለው ነው የአዲስ አበባ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ያስታወቀው፡፡ በቢሮው የስፖርት ዘርፍ ምክትል ቢሮ ኃላፊ አቶ ዳዊት ትርፉ ስለጉዳዩ ተጠይቀው፣ ‹‹ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባ ከሰው ልጆች ጤና በላይ ምን አለ?›› ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
ጉዳዩ የቅንጦት ነው፣ አላስፈላጊ ወጪና ቅድሚያ ሊሰጠው የማይገባ ነው መባሉን እንደማይቀበሉት አቶ ዳዊት ተናግረዋል፡፡ ‹‹ሠራተኛው በሚሠራበት ቦታ አካላዊ እንቅስቃሴ በማድረግ ንቁና ውጤታማ እንዲሆን ማስቻል፣ ከስፖርት ፖሊሲያችን ጋር የሚሄድና የሥራ ላይ ምርታማነትንም የሚያሳድግ ነው፤›› ብለዋል፡፡
በአገሪቱ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች እየተስፋፉ መሆናቸውን የተናገሩት አቶ ዳዊት፣ ‹‹ለመድኃኒት ግዥ የምናዋጣውን ውድ ምንዛሪ ለመቀነስ ብቻ ሳይሆን፣ ጤናማና ውጤታማ ሠራተኛን ለመፍጠር የጂምናዚየም ግንባታዎቹ ወሳኝ ጠቀሜታ አላቸው፤›› ብለዋል፡፡
የሚበላ ምግብ በጠፋበት አገር ጂምናዚየም በየወረዳው መገንባቱ አላስፈላጊ ነው በማለት ብዙዎች ፕሮጀክቱን ሲያጥላሉት ተሰምተዋል፡፡ ‹‹ይህ የተሳሳተ አመለካከት ነው፤›› ሲሉ የገለጹት አቶ ዳዊት፣ ‹‹ቻይናውያን ውሹ የተባለውን ባህላዊ ስፖርታቸውን ለጤና መጠበቂያነትና ለምርታማነት ተጠቅመውበታል፤›› ሲሉ አስረድተዋል፡፡