በተራዘመ ድርቅ ምክንያት እየተፈተነ ያለው የቦረና ዞን በተወሰኑ አካባቢዎች ላይ የጣለውን አነስተኛ መጠን ያለው ዝናብ ተከትሎ፣ በፈልፈሌና ዲሎ ወረዳዎች ላይ የአንበጣ ሥጋት እንደተጋረጠበት አስታወቀ፡፡
ባለፉት ተከታታይ የዝናብ ወቅቶች እርጥበት ያላገኘው የቦረና ዞን በሚያዝያ ወር መጀመርያ በተወሰኑ የዞኑ አካባቢዎች ላይ ዝናብ መዝነቡን የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ጃርሶ ቦሩ ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡ በዚህ ዝናብ መጠኑ አነስተኛ ቢሆንም ምርት መኖሩን ያስረዱት ዋና አስተዳዳሪው፣ ምርቱ ግን በወረዳዎቹ ባለው አንበጣ ምክንያት ጉዳት ይደርስበታል የሚል ሥጋት መኖሩን ገልጸዋል፡፡ አክለውም ‹‹በዝናም እጥረት ምክንያት ያልታረሰ ሰብል ችግር እየፈጠረ ነው፣ የበቀለው ሳርና እህልም በዚህ አንበጣ የሚጠፋ ከሆነ ድምሩ ኅብረተሰብ ላይ ችግር ያመጣል፤›› ብለዋል፡፡
የዞኑ ግብርናና የእንስሳት ልማት ቢሮም በበኩሉ በተለይ ፈልፈሌ ወረዳ ላይ ተገኝቶ ቁጥጥር ያልተደረገበት አንበጣ በመኖሩ፣ በአንበጣው ምክንያት የተከሰተው ሥጋት ‹‹ከፍተኛ›› መሆኑን አስታውቋል፡፡ የቢሮው ምክትል ኃላፊ ቃሲም ጉዮ (ዶ/ር)፣ ‹‹ፈልፈሌ ውስጥ የቀረ አለ፣ ሰብልም ያለው እዚያ አካባቢ ስለሆነ ሲወጣ በጣም ያጠፋል›› በማለት ተናግረዋል፡፡
እንደ ዞኑ ዋና አስተዳዳሪ ገለጻ በቦረና የአንበጣ ሥጋቱ የተከሰተው የአንበጣን ሁኔታ የሚከታተሉ የፌዴራል መንግሥት ቡድኖች በአካባቢው ሲያደርጉት የነበረው ክትትል በመቋረጡ ነው፡፡ አውሮፕላን በአማካይነት ሲደረግ የነበረው ክትትል መቋረጡን የተናገሩት አቶ ጃርሶ፣ በምድር የሚደረግ ክትትል የሚያስገኘው ውጤት አነስተኛ መሆኑን አክለዋል፡፡
የግብርና ሚኒስቴርም በአካባቢው ሲደረግ የነበረው የአንበጣ ክትትል መቋረጡን ያስረዳ ሲሆን፣ ለዚህም ሁለት ምክንያቶችን አስቀምጧል፡፡ ከዚህ ቀደም ሚኒስቴሩ አየርና በምድር አሰሳ ለማድረግ ቢሞክርም በአካባቢው ያለው የፀጥታ ሁኔታ ሥጋት መፍጠሩን በሚኒስቴሩ የዕፅዋት ጥበቃ ዳይሬክተር አቶ በላይነህ ንጉሴ ለሪፖርተር አስረድተዋል፡፡ በተጨማሪም ከዚህ ቀደም በምድር በተደረገ አሰሳ አንበጣው ያልተገኘ መሆኑንና በአካባቢው የአንበጣ መራቢያ ጊዜ ማለፉን በምክንያትነት አንስተዋል፡፡
‹‹አንበጣ የመራቢያ ጊዜው አልፏል ተብሎ የሚተው ነገር አይደለም፤›› ያሉት አቶ በላይነህ የፀጥታ ሁኔታው ላይ መሻሻል ካለ በሶማሌ ክልል የሚገኘውን የክትትል ቡድን ወደ ቦረና ማንቀሳቀስ እንደሚቻል ገልጸዋል፡፡