የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሙያ ሴቶች ማኅበር (ኢትመባሴማ) ከአሜሪካ ኢምባሲ ጋር በመተባበር፣ ለማኅበሩ ህልውና አስተዋጽኦ ላበረከቱ ለአንጋፋ አባላቱና አጋዦቹ የምሥጋናና የዕውቅና መርሐ ግብር አካሄደ።
ማክሰኞ ግንቦት 23 ቀን 2014 ዓ.ም. በራዲሰን ብሉ ሆቴል የተካሄደው መርሐ ግብር፣ ማኅበሩን ከምሥረታ ጀምሮ በአስቸጋሪም ሆነ በመልካም ጊዜ ጊዜያቸውን፣ ገንዘባቸውንና ዕውቀታቸውን ጨምሮ ላበረከቱት አስተዋጽኦ ዕውቅና የተሰጠበት ነው።
ማኅበሩን በነፃ ሲያገለግሉ የቆዩት ሁለት ቀደምት አባላት ማለትም ወ/ሮ ተካበች አሰፋና ወ/ሮ ሰሎሜ ደስታ፣ ከሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ደኤታ ወ/ሮ ዓለሚቱ ዑሚድ የክብር ካባና የምሥጋና የምስክር ወረቀት ተቀብለዋል።
ሴት ጋዜጠኞች በመገናኛ ብዙኃን ውስጥ ተቀጥረው ከመሥራት አልፈው ባለቤት የሆኑ እንዳሉ ያስታወሱት ወ/ሮ ዓለሚቱ፣ እነሱን በማኅበራዊ፣ በፖለቲካዊና በኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ላይ ማሳተፍ አስፈላጊ ነው ብለዋል።
ማኅበሩ ለሴት ጋዜጠኞች እያደረገ ያለው ጥረትና የፈጠረው የልምድ ልውውጥ ለሙያው ዕድገት አስተዋጽኦ ያደርጋል ሲሉ ሚኒስትር ደኤታዋ አስረድተዋል።
ማኅበሩ ለሴት ጋዜጠኞች እያደረገ ያለውን ዕገዛ መቀጠል እንደሚገባው ገልጸው፣ ሚኒስትር መሥሪያ ቤቱ ድጋፍ ያደርጋል ብለዋል።
ከዚህ በተጨማሪ ለማኅበሩ ቀጣይነት አስተዋጽኦ ላበረከቱት የመገናኛ ብዙኃን ምክር ቤት የሥራ አስፈጻሚ ሰብሳቢ፣ ለአቶ አማረ አረጋዊ፣ ለፎርቹን ጋዜጣ መሥራችና ማኔጂንግ ኤዲተር ለአቶ ታምራት ገብረ ጊዮርጊስ፣ ለኢቢኤስ ቴሌቪዥን መሥራች ለአቶ አማን ፍሰሐ ጽዮንና ለወ/ሮ ሶሎሜ ታደሰ ዕውቅና ተሰጥቷል።
ዕውቅና የተሰጣቸው ግለሰቦችም የምስክር ወረቀቱን በወሰዱበት ወቅት ባደረጉት ንግግር፣ በየተቋማቸው ሴት ጋዜጠኞች እንደሚገኙና ሙያዊ ዕገዛ እንደሚያደርጉላቸው ተናግረዋል።
በተጨማሪም የተሰጣቸው ዕውቅና ለወደፊት ሴቶችን ለማብቃት ትልቅ የቤት ሥራ እንደሚሆናቸው ተናግረዋል።
ከዚሁ ጋር በተያያዘ “ዘመነ ዲጂታል ለሴቶች በረከት ወይስ ተግዳሮት?” በሚል ርዕስ ሴት ጋዜጠኞች ውይይት አካሂደዋል።
በውይይቱ ላይ የማኅበሩ የሥራ አስፈጻሚ ቦርድ አባል የሸዋ ማስረሻ በአሁኑ ጊዜ እየተስፋፋ የመጣው የዲጂታል ሚዲያ፣ ለሴቶችና ለአካል ጉዳተኞች መልካም ዕድሎችን ይዞ ቢመጣም፣ በፆታቸው ምክንያት ለጥቃት ተጋላጭ መሆናቸውን ገልጻለች።
ጋዜጠኝነት አድሎአዊ አሠራሮችን መዋጊያ መሣሪያ መሆኑን የጠቆመችው የሸዋ፣ በተለያዩ መገናኛ ብዙኃን ውስጥ የሚሠሩ ሴቶች ለአድልኦ ተጋላጭ ናቸው ብላለች።
የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሙያ ሴቶች ማኅበር የሴት ጋዜጠኞችን አቅም ለማጎልበት በ1991 ዓ.ም. የተቋቋመ የሙያ ማኅበር ሲሆን፣ ላለፉት 22 ዓመታትም በርካታ የሥልጠናና የልምድ ልውውጦች ከአጋር ድርጅቶች ጋር በማካሄድ ሴት ጋዜጠኞችን የሚያግዝ ነው።